የዳውሮ ብሔር የዘመን መለወጫ “ቶኪ ቤኣ” በዓል በሰላም ማክበር እንዲቻል በፀጥታ በኩል ምንም ስጋት እንዳማይኖር ፖሊስ አሳሰበ

የቶኪ -ቤኣ በዓል በዳውሮ ብሔር ዘንድ በየዓመቱ በደማቅ ሁኔታ የሚከበር የዘመን መለዋጫ በዓል ነው።

የዘንድሮ በዓል ከነሐሴ 29 እስከ 30/2016 ዓ.ም ከተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች የአካባቢው ተወላጆችና እንግዶች በዞኑ ታርጫ ከተማ በድምቀት ይከበራል፡፡

በዳውሮ ዞን ፖሊስ መምሪያ ማህበረሰብ አቀፍ ወንጀል መከላከል ክፍል ኃላፊ ምክትል ኮማንደር አስናቀ ሀብቴ እንደገለጹት የቶኪ ቤኣ በዓል የብሔሩ የማንነት መገለጫ በዓል ሲሆን ይህን በዓል ከዋዜማው አንስቶ በሰላም ለማክበር እንዲቻል በቅንጅት ሲሠራ ቆይቷል።

ከዚህ ቀደምም ሕዝቡ ሰላምን አጽንቶ የያዘ በመሆኑ በዓሉን ለማክበር የሚመጡ እንግዶች በሰላም አክብረው እንዲመለሱ ማኅበረሰቡን ያሳተፈ ተግባር እየተከናወኑ ይገኛል።

በዞኑ በሁሉም አካባቢዎች በዓሉን ከማክበር ባለፈ የተለያዩ የቱሪስት መስህቦችን ጎብኝተው እንዲመለሱ በየደረጃው ከሚገኙ መዋቅሮች ጋር በቅንጅት እየተሠራ ይገኛልም ብለዋል።

የታርጫ ከተማ አስተዳደር ፖሊስ አዛዥ ኢንስፔክተር አረጋ ሳላሎም በበኩላቸው ከተማዋ ከክልሉ ብዙሃ ማዕከላት አንዷ እንደመሆኗ መጠን ከመቼውም ጊዜ በላይ ሰላምን ለማስጠበቅ በትጋት እየተሠራ ይገኛል ብለዋል።

ይህ ዕቅድ እንዲሳካ ለማድረግ ፖሊስ ብቻውን ሳይሆን ከህብረተሰቡ ጋር በመቀናጀት እንደሚሰራ አዛዡ ተናግረዋል ።

ያነጋገርናቸው የህብረተሰብ ክፍሎች በሰጡት አስተያየት በዓሉን ለማክበር የሚመጡ እንግዶችን በመልካም መስተንግዶ ተቀብለው ለማስተናገድ መዘጋጀታቸውን ገለፀዋል።

ዘጋቢ፡ አሸናፊ ግዛው- ከዋካ ቅርንጫፍ ጣቢያችን