የኦሞ ወንዝና የቱርካና(ሩደልፍ) ሐይቅ በአካባቢው ላይ በየዓመቱ የሚያስከትለውን ጉዳት ለማስቀረትና ዘላቂ መፍትሔ ለማበጀት የባለሙያ ምክረ ሐሳብ ጥናት እንደሚጠይቅ ተገለፀ

የኦሞ ወንዝ የፍሰት መዳረሻው ቱርካና (ሩደልፍ)ሐይቅ ሲሆን ከሐይቁ ጋር በመቀላቀል ወደ ኋላ በመመለስ በዳሰነች ወረዳ ነዋሪዎች ላይ ከፍተኛ አደጋ ደቅኗል፡፡

በብዙ ሚሊዮን ብር የሚገመት ቁሳቁስ ላይ አደጋ ማስከተሉን በሐይቁ አካባቢ በንግድ የሚተዳደሩ ባለሀብቶች ገልፀው የሚመለከታቸው አካላት መፍትሄው ዙሪያ እንዲሠሩ ጠይቀዋል።

በተለይ ከሐይቁ ነጭ አሳን በማውጣት ለሆቴሎች የሚያቀርቡት ባለሀብቶች ዛሬ ላይ ስራቸው ላይ አሉታዊ ተፅእኖ መፍጠሩንም ተናግረዋል ።

በሐይቁ አካባቢ ጉዳት ለደረሰባቸው አካላት ተረጋግተው ሥራቸውን እንዲያከናውኑ የዳሰነች ወረዳ አስተዳደር እየሠራ መሆኑን የወረዳው ዋና አስተዳዳሪ አቶ ታደለ ሀቴ ገልፀዋል።

ሐይቁ ደርሶባቸው ጉዳት ያስከተሉ ንብረቶችን ለማስወጣት ማሽነሪ እንደምላክና ነዋሪዎችም ተለዋጭ በ ቦታ ላይ እንዲሆኑ ይደረጋል ሲሉም አስተዳዳሪው አስረድተዋል።

የወንዙ ሙላት በየጊዜው ባህርውን በመቀያየር የመሬት መሰንጠቅና የውሃ መከላከያ ካብ በመደርመስ ወደ ኦሞራቴ እየተጠጋ በመሆኑ ተጨማሪ ማሽነሪዎች ከክልሉ እንዲመጡ ተደርጓል ብለዋል አቶ ታደለ።

በተለይ የማሽነሪና ነዳጅና የማሟላት ሁኔታው ፈታኝ መሆኑን ገልፀው የሚመለከታቸው አካላት ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል ።

ግብረ ሀይል ተቋቁሞ ክትትል እንዲያደርጉ የተሰየመ ሲሆን የግብረ ሀይሉ ሰብሳቢና የደቡብ ኦሞ ዞን መስኖና ቆላማ አካባቢ ልማት ጽ/ቤት ሀላፊ አቶ ብርሃኑ አረጋ ውሃው ሞልቶ የሚያስከትለውን ጫና ለመቀነስ በተቀናጀ መልኩ ርብርብ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል።

በሁለት አቅጣጫዎች ውሃውን የማስተንፈስ ሥራ እየተከናወነ እንደሚገኝም አቶ ብርሃኑ ገልፀዋል።

ዘጋቢ: ተመስገን አበራ-ከጂንካ ጣቢያችን