መንግስት አለአግባብ ዋጋ በሚጨምሩ አካላት ላይ የጀመረውን ቁጥጥር እንዲያጠናክር የታርጫ ከተማ ነዋሪዎች ጠየቁ

የታርጫ ከተማ አስተዳደር ንግድ፣ ኢንዱስትሪና ገበያ ልማት ጽ/ቤት በበኩሉ አግባባ ያልሆነ የዋጋ ጭማሪ በሚያደርጉት የንግድ ተቋማት ላይ እርምጃ እየወሰደ መሆኑን አስታውቋል፡፡

በታርጫ ከተማ አግኝተን ካነጋግረናቸው ሸማቾች መካከል ወ/ሮ አሞሬ ወንድሙ፣ ወ/ሮ መሠለች ዱረቶ፣ አቶ ባፈና በቀለ እና ሌሎችም በሰጡት አስተያየት የፍጆታ ዕቃዎች ዘይት፣ ሽንኩርት፣ ስኳር፣ ዱቄትን ጨምሮ አጠቃላይ ሸቀጣሸቀጦችና የፋብሪካ ምርቶች ላይ የታየው የዋጋ ጭማሪ እንዳሳሰባቸው ተናግረዋል።

አሁን የሚመለከታቸው አካላት ባደረጉት ክትትልና ቁጥጥር የተወሰኑ ንግድ ተቋማት ላይ እርምጃ በመወሰዱ የዘይት ዋጋ መስተካከሉን የተናገሩት ሸማቾች ቁጥጥርና ክትትሉ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቀዋል፡፡

ካነጋገርናቸው ነጋዴዎች መካከል መንግሥቱ ማሞ፣ እሸቱ ጎበናና ሌሎችም በሰጡት አስተያየት ከነጋዴዎች መካከል አንዳንዶች አላግባብ ጭማሪ እያደረጉ ይገኛሉ።

እነሱ ግን እንደሚሉት በዓልን አልያም ሌሎች ምክንያት እየፈጠርን በሸማቾች ላይ ዋጋ አንጨምርም በማለት ለጣቢያችን ተናግረዋል።

የታርጫ ከተማ አስተዳደር ንግድ፣ ኢንዱስትሪና ገበያ ልማት ሃላፊ አቶ መንግስቱ ይመኑም በበኩላቸው በህጋዊ መንገድ የሚሠሩ ነጋዴዎች እንዳሉ ሁሉ በተቃራኒው የግል ጥቅማቸውን ብቻ ለማሟላት የዋጋ ጭማሪ የሚያደርጉም አሉ ብለዋል፡፡

450 የሚጠጉትን የተለያዩ የንግድ ተቋማት ላይ ቁጥጥር መደረጉን፣ የዋጋ ዝርዝር ያለጠፉትን፣ ምርቱት በመጋበዝ አከማችተው አውጥተው የማይሸጡትን፣ እንዲሁም ዋጋ አለአግባብ ጨምረው በሚሠጡና በሌሎችም ህገዊ ባልሆነ መንገድ በሚንቀሳቀሱ 68 የንግድ ተቋማትን ላይ የማሸግ እርምጃ ወስደናል ብለዋል።

ከዚህም ጎን ለጎን የዘመን መለዋጫ በዓል መቃረቡን ተከትለው የፍጆታ ዕቃዎችን በሸማቾች ማህበር ለማስገባት እንቅስቃሴ መጀመሩን አቶ መንግሥቱ ተናግረዋል።

ዘጋቢ፡ አሸናፊ ግዛው – ከዋካ ጣቢያችን