የሆሳዕና እናት ቃለ ህይወት ቤተክርስቲያን አዲሱን ዓመት ምክንያት በማድረግ ከአንድ መቶ በላይ ለሚሆኑ አቅመ ደካሞች የምግብ ቁሳቁስ ድጋፍ አደረገች
ቤተክርስቲያኗ ለበርካታ አቅመ ደካሞች ጊዜያዊና ቋሚ ድጋፍ እንዲሁም ከ70 በላይ ለሚሆኑ አቅም ላነሳቸው ዜጎች ቋሚ የስራ እድል በመፍጠር መልሶ ማቋቋም መቻሏም ተገልጿል።
የሆሳዕና እናት ቃለ ህይወት ቤተክርስቲያን ሰብሳቢ አቶ ደሳለኝ ግርማ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የተቸገሩትን መርዳት እና መደገፍ ከእምነቱ አስተምህሮዎች መካከል በመሆኑ በተለያዩ ጊዜያት ተመሳሳይ ድጋፎች በቤተ ክርስቲያኗ ሲደረጉ ቆይቷል።
ከሰባት ዓመታት ወዲህ ተቋቁሞ የተለያዩ በጎ አገልግሎቶችን እያከናወነ በሚገኘው በፍቅርና ርኅራኄ አገልግሎት ህብረት አስተባባሪነት ከምዕመናን የተሰበሰበ የአልባሳት እና የምግብ ቁሳቁስ በዕለቱ ለአቅመ ደካሞች መስጠት መቻሉንም ገልጸዋል።
ከአልባሳት ውጪ አምስት መቶ ሺ ብር የሚገመት የምግብ ቁሳቁስ ለአቅመ ደካሞች የተዘጋጀ ሲሆን በዕለቱም ለአንድ መቶ አስር ዜጎች ዘይትና ዱቄት መሰጠቱን ተናግረዋል። ድጋፉ የሚቀጥል መሆኑን በመጥቀስ።
ወጣት ሙሉ ጸጋ ተስፋዬ የፍቅርና ርህራሄ አገልግሎት ህብረት መሪ ሲሆን ህብረቱ ከተቋቋመበት ከሰባት ዓመታት ወዲህ በተለያዩ ጊዜያት በጎ ተግባራትን ሲያደርግ መቆየቱን ተናግሯል።
በፍቅርና ርኅራሄ ሌሎችን መርዳትና ማገልገል የቤተ ክርስቲያን አንዱ ተልዕኮ እንደመሆኑ መጠን ከጎዳና ህፃናት እስከ አረጋዊያን ድረስ ለተቸገሩ ዜጎች ጊዜያዊ ድጋፍ ከማድረግ ባለፈ ከተረጂነት ወጥተው ራሳቸውን በዘላቂነት ማቋቋም የሚችሉበትን የስራ መስኮች የማመቻቸት ስራ ስለመስራቱም የህብረቱ መሪ ወጣት ሙሉ ፀጋ አብራርቷል።
በተጨማሪም የ75 ተማሪዎችን ሙሉ የትምህርት ወጪ በቋሚነት በመሸፈን በግልና በመንግስት ትምህርት ቤቶች እንዲማሩ መደረጉን የተነገረ ሲሆን የቤት ኪራይ ወጪ የሚሸፈንላቸው አረጋዊያን እና አካል ጉዳተኞች መኖራቸውም ተገልጿል።
ድጋፍ የተደረገላቸው የህብረተሰብ ክፍሎች በበኩላቸው፤ በዕለቱ ከተደረገላቸው ድጋፍ ባሻገር የልጆቻቸውን የትምህርት ወጪ በመሸፈን እያደረጉ ላለው ሰብዓዊ ተግባር አመስግነዋል።
ድጋፉ የሚደረግላቸው ዜጎች ራሳቸውን ከተረጂነት ለማላቀቅ የተለያዩ ስራዎችን በመስራት እንዲለወጡ በቤተክርስቲያኗ በኩል ግንዛቤ እንደሚሰጥም ተገልጿል።
ዘጋቢ፡ ኤርጡሜ ዳንኤል – ከሆሳዕና ጣቢያችን

More Stories
የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል በብልፅግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት የፖለቲካና አቅም ግንባታ ዘርፍ እና የአደረጃጀት ዘርፍ የ2018 በጀት አመት አፈጻጸምና የ2019 በጀት ዕቅድ ዙሪያ በታርጫ ከተማ ውይይት እየተካሄደ ነው
ኦሞ ባንክ ሳውላ ዲስትሪክት በ2018 በጀት ዓመት ከ86 ሚሊዮን ብር በላይ የተጣራ ቁጠባ ማስመዝገቡን ገለጸ
እየተካሔደ ያለው ሀገራዊ ምክክር በሀገሪቱ አንድነት እና ሠላም ለማስፈን ፋይዳው የጎላ መሆኑን የአርባምንጭ ከተማ ነዋሪዎች ተናገሩ