በቡርጂ ዞን ከፌደራልና ከክልል የህዝብ ተወካዮች ጋር የውይይት መድረክ እየተካሄደ ይገኛል

የዞኑ ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባዔ ወ/ሮ ወለቱ ዋዮ መድረኩን በንግግር በከፈቱበት ወቅት ከዚህ ቀደም ከህብረተሰቡ ሲነሱ የቆዩ የመልካም አስተዳደር ችግሮች፣ የሰላም እጦት፣ የመልማት ጥያቄዎችና ሌሎችም ተያያዥ ጉዳዮች ደረጃ በጀረጃ ቀርበው ምላሽ ይሰጥባቸዋል ነው ያሉት፡፡

በኢፌዲሪ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የቡርጂ ህዝብ ተወካይ አቶ ከድር መሐመድ ከህብረተሰቡ የሚነሱ ጥያቄዎችን በመውሰድ ጥያቄዎቹ በሚፈቱበት አግባብ በየደረጃው ለሚገኙ ባለድርሻዎች ይቀርባሉ ብለዋል፡፡

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት የቡርጂ ዞን ተወካይ አቶ ማሬ አልማየሁ በውይይት መድረኩ በሁለም ዘርፍ የሚስተዋሉ ችግሮችን ለይቶ በመገምገም ለሚመለከታቸው አካላት ለማቅረብ የህዝቡ ውይይት ወሳኝ መሆኑን ጠቁመው ሁሉም የድርሻውን እንዲወጣ አሳስበዋል፡፡

ከመድረኩ ተሳታፊዎች መካከል አቶ አደን ማዶና ደስታ እማሌ በሰጡት አስተያየት በዞን ደረጃ የሚስተዋለው የሰላም ጉዳይ፣ የመንገድ፣ የመብራት፣ የኔትወርክና የውሃ ችግሮች ሁሌም ከህብረተሰቡ የሚነሱና እልባት ያላገኙ እንደሆነ በማንሳት የህዝብ ተወካዮችም ችግሮችን ለመፍታት እንዲሠሩ ጠይቀዋል፡፡

ዘጋቢ፡ ዮሴፍ ቶልኬ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን