በገደብ ከተማ የተለያዩ ግንባታዎች ተጠናቀው ለአገልግሎት በቁ

ሀዋሳ፡ ነሐሴ 242016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በጌዴኦ ዞን በገደብ ከተማ የተለያዩ ግንባታዎች ተጠናቀው ለአገልግሎት መብቃታቸውን ከተማ አስተዳደሩ አስታውቋል፡፡

በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት ከተማ አስተዳደሩ ያጠናቀቃቸውና በመጠናቀቅ ላይ ያሉ ፕሮጀክቶች በዞኑ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች እና በምክር ቤት አባላት ተጎብኝቷል።

የከተማው ምክር ቤትን ጨምሮ አንዳንድ በገደብ ከተማ አስተዳደር ሥር የሚገኙ ሴክተር መሥሪያ ቤቶች የግለሰቦችን ቤት በመከራየት ለተገልጋዩ ምቹና ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት እየተቸገሩ መሆናቸውን የገደብ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ታሪኩ ሮቤ አስታውቀዋል፡፡

ችግሩን ለመቀነስ በተሠራው ሥራ የሴቶችና ህፃናት ጉዳይ ጽ/ቤት ቢሮ ከሁለት ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ግንባታው ተጠናቀቆ ለአገልግሎት መብቃቱን የጠቆሙት ከንቲባው በቀጣይም ከ4 ነጥብ 7 ሚሊዮን ብር በላይ ግንባታው እየተፋጠነ የሚገኘውን የከተማ ፖሊስ ጽ/ቤት ፈጥኖ በማጠናቀቅ አላስፈላጊ የመንግስት ሀብት ብክነትን ለማስቀረት በትኩረት እንደሚሠራ አስረድተዋል፡፡

በሌላ በኩል የህብረተሰቡ የዘመናት ጥያቄ ሆኖ የቆየውና ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳው ከፍተኛ የሆነ የጂጌቲ ድልድይ ግንባታ ከአንድ ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ተገንብቶ ለአገልግሎት ክፍት መሆኑን ገልጸዋል፡፡

የጌዴኦ ዞን ብልጽግና ፓርቲ ጽ/ቤት ኃላፊ እና የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ አበባየሁ ኢሳያስ ህዝብና መንግስት የሰጣቸውን አደራ በአግባቡ እየተወጡ ከሚገኘው የገደብ ከተማ አስተዳደር ተሞክሮ በመውሰድ ሌሎች መዋቅሮችም እንዲጠናከሩ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡

ያነጋገርናቸው የከተማው ነዋሪዎች ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የህዝቡን ጥያቄ አድምጦ ተግባራዊ ምላሽ የሚሰጥ አመራር በመፈጠሩ መደሰታቸውን ተናግረዋል፡፡

ዘጋቢ: ሳሙኤል በቀለ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን