ሀዋሳ፡ ነሐሴ 24/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል አጀንዳ ማሰባሰብ ስራውን ነገ እንደሚጀምር አስታውቋል።
የአጀንዳ ማሰባሰቡን ተግባር ቅዳሜ ነሐሴ 25 ቀን 2016 ዓ.ም ጀምሮ ለስድስት ተከታታይ ቀናት እንደሚያካሂድ የገለጹት፥ የኮሚሽኑ ኮሚሽነር ዶክተር ዮናስ አዳዬ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በሆሳዕና ከተማ መግለጫ ሰጥተዋል።
ኮሚሽኑ ቀደም ሲል በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በአጀንዳ ማሰባሰብ የሚሳተፉ ተወካዮች እንዲመረጡ ማድረጉንም ዶክተር ዮናስ ገልጸዋል።
በአጀንዳ ማሰባሰብ ሂደቱ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የተመረጡ የህብረተሰብ ተወካዮች እና ባለድርሻ አካላትን የወከሉ ከ82 ወረዳዎች የተመረጡ ከ1ሺህ 5 መቶ በላይ ተወካዮች እንደሚሳተፉም ዶክተር ዮናስ አመላክተዋል።
በህዝቦች መካከል ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን ምክክርን ባህል በማድረግ እየሰራ መሆኑንም ኮሚሽነር ዶክተር ዮናስ አዳዬ ጠቁመዋል::
በአጀንዳ ማሰባሰብ ሂደቱ ከተለያዩ ወረዳዎች የተውጣጡ የህብረተሰብ ተወካዮች፣ የፖለቲካ ፓርቲ ተወካዮች፣ የሶስቱ የመንግስት አካላት ተወካዮች፣ የተለያዩ ተቋማት እና ማህበራት ተወካዮች እንዲሁም ታዋቂ እና ተፅዕኖ ፈጣሪ ግለሰቦች ተወካዮች እንደሚሳተፉ ይጠበቃል።
በምክክሩ ሁሉም አሸናፊዎች የሚሆኑበት ሂዳት እንዲፈጠር ዜጎች ኃላፊነታቸውን በተገቢ መወጣት እንዳለባቸው ዶክተር ዮናስ ጠቅሰዋል::
ኮሚሽኑ የክልሉ ነዋሪዎች በአጀንዳ ማሰባሰብ ሂደቱ በንቃት እንዲሳተፉ እና አስፈላጊውን ትብብር እንዲያደርጉም ጥሪ አቅርበዋል።
በቀጣይ ለሀገር ደረጃ ለሚቀርብ ብሔራዊ ውይይት እንደ ማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ከከፍተኛ የመንግስት መዋቅር ጀምሮ ከተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ከተውጣጡ የህብረተሰብ ክፍሎች ጋር ከነገ ጀምሮ የተሳካ ውይይት በማድረግ ለሀገራዊ ምክክክር ተገቢ ግብዓት እንደምናገኝ ሙሉ ተስፋ አለን ሲሉም ገልፀዋል።
ዘጋቢ: አማኑኤል አጤቦ – ከሆሳዕና ጣቢያችን

More Stories
የአስተሳሰብና የተግባር አንድነት በማጠናከር ክልላዊ አንድነትን ማጎልበት እንደሚገባ ተገለጸ
ህዝበ ሙስሊሙ የመውሊድ በዓልን ሲያከብር በብዝሃነት ውስጥ የሚንፀባረቁ የመረዳዳትና የአብሮነት በጎ እሴቶችን ይበልጥ በማጠናከር ሊሆን እንደሚገባ ተገለጸ
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ብልፅግና ፓርቲ ኃላፊና የየዞን ከፍተኛ አመራሮች በሣውላ ማረሚያ ተቋም አረንጓዴ አሻራቸውን በማኖር ልዩ ልዩ የልማት ሥራዎችን ጎበኙ