ገቢን አሟጦ መሰብሰብ እንደሚገባ ተገለጸ

ሀዋሳ: ነሐሴ 24/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) ገቢን አሟጦ መሰብሰብ እንደሚገባ የአሪ ዞን አስተዳደር አስታወቀ።

የዞኑ ገቢዎች መምሪያ ከዞን ማዕከል፣ ወረዳዎችና የከተማ አስተዳር ባለድርሻ አካላት ጋር በገቢ ተግባራት ዙሪያ በጂንካ ከተማ ውይይት እያደረገ ይገኛል።

በመድረኩ የተገኙት የዞኑ ገቢዎች መምሪያ ኃላፊ አቶ ሕዝቀለሰ ጋርታ ላለፉት ተከታታይ ጊዜያት የዞኑ ገቢ አፈፃፀም መሻሻል ማሣየቱን ጠቅሰው የገቢ አሰባሰቡን ማዘመን፣ የግብር ከፋዩ ግንዛቤ መሻሻልና የባለድርሻ ቅንጅታዊ አሰራር ለአፈፃፀሙ መሻሻል ምክንያት እንደነበር አመላክተዋል።

በ2017 በጀት አመት አንዳንድ በዘርፉ የሚስተዋሉ የአመለካከትና አፈፃፀም ችግሮችን በመቅረፍ በአጠቃላይ ከ876 ሚሊዮን 471ሺህ ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ እየተሠራ እንዳለ አመላክተዋል።

መድረኩን በንግግር የከፈቱት የአሪ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብረሃም አታ ለልማትና መልካም አስተዳደር ጉዳዮች ምላሽ ለመስጠት የውስጥ ገቢ አቅምን አሟጦ መሰብሰብ ወሳኝ በመሆኑ በቀጣይ በዞኑ ያሉ የገቢ ባለድርሻ አካላት ትኩረት ሰጥተው ሊሰሩ ይገባል ብለዋል።

ዘጋቢ: መልካሙ ቡርዝዳቦ – ከጂንካ ጣቢያችን