አዳዲስ የሰብል ዝርያዎችን በማላመድ ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ እንደሚገባ የጉራጌ ዞን ግብርና መምሪያ አስታወቀ

በዞኑ አበሽጌ ወረዳ በኩታ ገጠም የለማ የሩዝ ማሳ የመስክ ጉብኝት ተካሂዷል።

በጉራጌ ዞን አበሽጌ ወረዳ በ1መቶ 80 ሄክታር መሬት በኩታ ገጠም የለማው የሩዝ ማሳ ከዚህ ቀደም በአካባቢው በብዛት ያልተለመደና ከቅርብ ዓመታት ወዲህ አበረታች ምርት እየሰጠ ያለ መሆኑን የቀበሌው አርሶአደሮች ተናግረዋል።

የመፈልፈያ ማሽን፣ የግብዓት እጥረት እንዲሁም የገበያ ትስስር ከመፍጠር ረገድ ተግዳሮቶች እንዳሉ የተናገሩት አርሶአደሮቹ ችግሮቹ ቢቀረፉ ይበልጥ ውጤታማ መሆን እንችላለን ብለዋል።

የጉራጌ ዞን የግብርና መምሪያ ምክትል ሀላፊ አቶ አክሊሉ ካሳ፤ በዞኑ የሩዝ ምርት በኩታ ገጠም ሲሰራ የመጀመሪያ ነው ያሉ ሲሆን በሌሎችም ወረዳዎች ተሞክሮ በመውሰድ መሰራት ይኖርበታል ብለዋል።

በአርሶ አደሩቹ የተነሱ ችግሮችም ከአጋዥ ተቋማት ጋር በመቀናጀት እንደሚቀረፍ አመላክተዋል።

የአበሽጌ ወረዳ ዋና የመንግስት ተጠሪ አቶ ሙሉጌታ ፈቀደ ሩዝ ተኪ ምርት በመሆኑ በትኩረት በመስራት በኩታ ገጠም ማልማት መቻሉን አስረድተዋል።

ከነበረው የግብዓት እጥረት አንፃር ችግሮች ቢስተዋሉም ያለውን በፍትሃዊነት በመጠቀም ውጤታማ ስራ መሰራቱን ጨምረው ገልጸዋል።

ወረዳው በብዙ ሰብሎች ውጤታማ ነዉ ያሉት የወረዳው የግብርና ጽ/ቤት ተወካይ አቶ ሙላት ደሳለኝ፤ ከዚህ ቀደም እንደሙከራ በተጀመረው የሩዝ ምርት የአርሶአደሩን ውጤታማነት በማየት የማስፋት ስራ መሰራቱን ተናግረዋል።

የወልቂጤ ግብርና ምርምር ማዕከል ዳይሬክተር አቶ ቤቴል ነክር በበኩላቸው የአካባቢው አፈርና አየር ንብረት ለሩዝ ምርት ተስማሚ መሆኑን ተናግረው ይበልጥ ምርታማ ለመሆንም ለአካባቢው ተስማሚ የሆኑ ዝርያዎችን በመለየት አርሶአደሩን በቅርበት የማገዝ ስራ በትኩረት ይሰራል ነው ያሉት።

ዘጋቢ፡ አስረስ ንጋቱ – ከወልቂጤ ጣቢያችን