የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ከመስተዳድር ምክር ቤት አባላት ጋር የዕቅድ ግብ ስምምነት ተፈራረሙ

ሀዋሳ፡ ነሐሴ 13/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል መስተዳድር ምክር ቤት አባላት በ18ኛ መደበኛ ስብሰባው ከክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ እንዳሻው ጣሰው ጋር የ2017 በጀት ዓመት የዕቅድ ግብ ስምምነት ተፈራርመዋል።

የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ እንዳሻው ጣሰው በተገኙበት የተካሄደው 18ኛው የመስተዳድር ምክር ቤት ስብሰባ፥ የአንድ አመቱን ጉዞ ትውስታ ምን ይመስል እንደነበር ሰነድ ቀርቦ የአመቱን አፈጻጸም በማየት ተጀምሯል።

መስተዳድር ምክር ቤቱ የ2017 ዕቅድ ማጠቃለያ ላይ በዝርዝር የመከረ ሲሆን፥ በተለይ በዕቅድ ሊካተቱና ሊሻሻሉ ይገባቸዋል ብሎ ከዚህ ቀደም በዕቅድ ግምገማ ወቅት በሰጠው ግብረ መልስ መሠረት ማስተካከያ የተደረገበትን የ2017 ዕቅድ ማጠቃለያ የግብ ስምምነት በክልሉ የፕላንና ልማት ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር ባዩሽ ተስፋዬ ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል።

ሴክተር መስሪያ ቤቶች በ2017 በጀት አመት ዕቅድ ዙሪያ የፈጻሚ ማዘጋጃ መድረክ በማካሄድ በተቋማት ዋና ዋና ግቦች ላይ ከፈጻሚዎቻቸው ጋር የጋራ መግባባት ላይ መድረስ እንደሚገባ ያሳሰቡት ርዕሰ መስተዳድር አቶ እንዳሻው ጣሰው፥ ስራውን ለመስራት የሚያስችል ከባቢ መፍጠር እና ከመስሪያ ቤት ባለድርሻ አካላት ጋር መወያየት እንደሚገባ ርዕሰ መስተዳድሩ አሳስበዋል።

የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል መስተዳድር ምክር ቤት አባላት የ2017 በጀት ዓመት ዕቅድ ግብ ስምምነት ከርዕሰ መስተዳድር አቶ እንዳሻው ጣሰው ጋር ተፈራርመዋል።

ዘጋቢ፡ ዘላለም ተስፋዬ