በጉራጌ ዞን የአበሽጌ ወረዳ አርሶ አደሮች የምርጥ ዘር ብዜት ተግባር በማከናወናቸው  ተጠቃሚነታቸው  እየጨመረ  መምጣቱን ተናገሩ

በዘንድሮው በ2016/17 የምርት ዘመን በበልግና በመኸር እስከአሁን ከ41ሺ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች በዘር መሸፈኑን የወረዳው አስተዳደር አስታውቋል።

በጉራጌ ዞን የአበሽጌ ወረዳ ካነጋገርናቸው አርሶ አደሮች መካከል ኑረዲን አብዱል ሽኩርና ዳዊት አሰፋ ይገኙበታል።

በሰጡት አስተያየትም በበልግና መኸር በኩታ ገጠም በማምረት ለምርጥ ዘር አቅራቢ ድርጅቶች ምርጥ ዘር እያቀረቡ ነው።

ለዚህም ውጤታማነት በባለድርሻ አካላት በኩል እየተደረገላቸው የሚገኘው ድጋፍ እና ክትትል ትልቅ አስተዋፅኦ እንዳበረከተላቸው ነው አርሶ አደሮቹ የገለፁት።

የአበሽጌ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ካሡ ጁሃር በዘንድሮው በ2016/17 የምርት ዘመን በበልግና በመኸር ከ60ሺ በላይ ሄክታር መሬት ለማልማት ታቅዶ እስካሁን ከ41ሺ ሄክታር በላይ በተለያዩ ሰብሎች ሲለማ አብዛኛው በኩታ ገጠም አስተራረስ የተተገበረ መሆኑ በማመላከት ቀሪው ማሳ በጤፍና ሽምብራ የሚሸፈን እንደሆነም ገልፀዋል።

የምርጥ ዘርና ማዳበርያ ግብዓትን ተደራሽ ለማድረግ በትኩረት መሠራቱን የገለፀት ዋና አስተዳዳሪው በቀሪ ጊዜያትም ግብዓትን በፍትሃዊነት የማዳረስ ስራ ይሰራል ብለዋል።

ዝናብ መዘግየቱን ተከትሎ በበልግ ከታረሰው 2ሺ ሄክታር ማሳ ዳግም በመዘራቱ አርሶ አደሩ፣ ባለሙያውና አመራር በጋራ መሥራት በመቻላቸው የተዘራው ሰብል አሁን ላይ በጥሩ ቁመና ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል።

ዘጋቢ፣ አማረ መንገሻ