የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የፓርላማ አባላትና የክልሉ የህዝብ ተወካዮች ም/ ቤት አባላት በጋራ የሚያከናውኑትን የህዝብ ውክልና ስራ በማስመልከት ውይይት እያደረጉ ነው

ሀዋሳ፡ ነሐሴ 10/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የፓርላማ አባላትና የክልሉ የህዝብ ተወካዮች ም/ ቤት አባላት በጋራ የሚያከናውኑትን የህዝብ ውክልና ስራ በማስመልከት ውይይት በማድረግ ላይ መሆናቸው ተመላክቷል፡፡

የህዝብ ተወካዮቹ በቀጣይ ቀናት ወደ ምርጫ ክልሎቻቸው በመንቀሳቀስ ከነዋሪዎች ጋር ውይይት እንደሚያደርጉ የሚጠበቅ ሲሆን ውይይቱ የህዝቡን የመልማት ጥያቄዎች አሁናዊ ሁኔታ ይፈተሻል።

በዚህ ወቅት ንግግር ያደረጉት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ወ/ሮ ፋጤ ሰርሞሎ ባለፈው የካቲት ወር 22ሺ 800 የህብረተሰብ ክፍሎች ከተወካዮቻቸው ጋር መወያየታቸውን ጠቁመዋል።

በነበረው ህዝባዊ ውይይት በርካታ የመልማት ጥያቄዎች ተነስተው የነበረ ሲሆን የምክር ቤቱ አባላት የአፈፃፀማቸውን ደረጃ ሲከታተል መቆየቱን አብራርተዋል።

የዛሬው መድረክም ለቀጣይ የህዝብ ውክልና ስራ በጋራ መስራት በሚቻልበት ሁኔታ የሚመክርና አጠቃላይ የህዝቦች ጥያቄ እና የተሰጡ ምላሾችን የሚፈትሽ ስለመሆኑ አመላክተዋል።

ዘጋቢ: ባዬ በልስቲ