ሰው ተኮር አገልግሎት አሠራር በተጨባጭ ውጤት እንዲያስመዘግብ በልዩ ትኩረት እየተሠራ መሆኑ ተገለፀ

ሀዋሳ፡ ነሐሴ 06/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) አገልግሎት ፈላጊው ህዝብ በተገቢው መንገድ መስተናገድ እንዲችልና ሰው ተኮር አገልግሎት አሠራር በተጨባጭ ውጤት እንዲያስመዘግብ በልዩ ትኩረት እየሰራ መሆኑን የኣሪ ዞን ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ገለፀ።

የዞኑ ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት የመልካም አስተዳደር ንቅናቄ መድረክ ማካሔድ ጀምሯል።

መድረኩን አስመልክቶ ማብራሪያ የሰጡት የኣሪ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብርሃም አታ ፓርቲው ሰው ተኮር ስራዎችን በስፋት እያካሄደ እንደሚገኝ ገልፀዋል።

ብልጽግና ፓርቲ በስራ ሂደት ያሉ ጉድለቶችን በማረም በምርጫ ወቅት ይሁንታ ለሰጠው ህዝብ፥ አዳዲስ ዕቅዶችን በመንደፍ እየተገበረ እንዳለ አቶ አብርሃም አስረድተዋል።

ከጊዜ ወደ ጊዜ በረቀቀ መልኩ እየተሰተዋለ ያለው ሌብነትና ብልሹ አሠራሮች ከመቸውም ጊዜ በላይ ተቀርፎ ለህዝቡ ልማት በቁርጠኝነት እየተሠራ ይገኛል ብለዋል።

መድረኩ ሰው ተኮር የልማት ሥራዎች በምን አግባብ ተፈፃሚ እየሆኑ ስለመሆናቸው በስፋት ዳስሶ የጋራ አቅጣጫ የሚያዝበት ነው ያሉት መድረኩን የሚሙሩት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መስኖና ቆላማ አካባቢ ልማት ቢሮ ሀላፊ አቶ ታረቀኝ ሐብቴ ናቸው።

መንግስት ሁሉም አገልግሎት ፈላጊው በተገቢው መንገድ መስተናገድ እንዲችል አሠራር ዘርግቶ እየሠራ የሚገኝ ሲሆን በዚህ ሂደት ያሉ ብልሹ አሠራሮች እንዲፈቱ በቁርጠኝነትና በትኩረት አመራሩ ሀላፊነቱን መወጣት አለበት ሲሉም አቶ ታረቀኝ አሳስበዋል።

ውጤታማና ቀልጣፋ አገልግሎት ለሀገር ግንባታ ወሳኝ ስለመሆኑም ተገልጿል ።

መድረኩ በተለያዩ ጉዳዮች እየመከረ ይገኛል።

ዘጋቢ: ተመስገን አበራ – ከጂንካ ጣቢያችን