ለውጦችን አጠናክሮ ማስቀጠል ይገባል- አፈ ጉባኤ ልክነሽ ሰርገማ

ለውጦችን አጠናክሮ ማስቀጠል ይገባል- አፈ ጉባኤ ልክነሽ ሰርገማ

ሀዋሳ፡ ነሐሴ 01/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የጉራጌ ዞን ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ወ/ሮ ልክነሽ ሰርገማ በሀገራችን በኢኮኖሚያዊ፣ በማህበራዊና በፖለቲካዊ ዘርፎች ተሰርተው የመጡ ለውጦችን አጠናክሮ ማስቀጠል ይገባል ብለዋል።

የጉራጌ ዞን ምክር ቤት 4ኛ ዙር 11ኛ አመት 26ኛ መደበኛ ጉባኤውን በወልቂጤ ከተማ እያካሄደ ይገኛል

ምክር ቤቱ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጎፋ ዞን ገዜ ጎፋ ወረዳ በተከሰተው የመሬት ናዳ ህይወታቸውን ላጡ ወገኖች የህሊና ጸሎት በማድረግ ነው ጉባኤውን የጀመረው።

የምክር ቤቱ አፈ ጉባኤ ወ/ሮ ልክነሽ ሰርገማ በ2016 በጀት ዓመት የዞኑ ምክር ቤት የተጣለበትን ሃላፊነት በመወጣት ጠንካራ የክትትል ተግባር በማከናወን እና ልዩ ድጋፍ በማድረግ ለውጦች መመዝገባቸውን ተናግረዋል።

በተለይም ከሰላምና ጸጥታ አንጻር የመጡ ጅምር ለውጦችን አጠናክሮ ማስቀጠል ከሁሉም ባለድርሻ አካላት የሚጠበቅ ተግባር መሆኑንም ጠቁመዋል።

በዞኑ በተለያዩ ዘርፎች በተሰሩ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎች ጥሩ አፈጻጸም ማስመዝገብ መቻሉ የሚበረታታ ቢሆንም ከህብረተሰቡ የመልማት ፍላጎትና አንጻር በቀጣይ ብዙ ስራ መስራት ይጠይቃል ሲሉ ተናግረዋል።

ምክር ቤቱ በቆይታው የጉራጌ ዞን አስተዳደር ምክር ቤት የ2016 በጀት እቅድ አፈጻጸም ሪፖርት አድምጦ ከተወያያ በኋላ ያጸድቃል፡፡ የ2017 በጀት ዓመት በጀትጠቋሚ እቅድ ተወያይቶ ማጽደቅና የተለያዩ ሹመቶችን መርምሮ እንደሚያፀድቅ ከወጣው መርሃ ግብር መረዳት ተችሏል።

ዘጋቢ፡ አስቻለው አማረ- ከወልቂጤ