በቤንች ሸኮ ዞን የትራፊክ አደጋን ለመከላከል የሚያስችሉ የተጠናከረ ስራ በቅንጅት እየሰራ መሆኑን የዞኑ ፖሊስ ገለፀ

የዞኑ ፖሊስ መምሪያ ህግን ተላልፈው ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ከ360 በላይ የባለሁለትና ባለሶስት እግር ተሽከርካሪዎችን በአንድ ሳምንት በቁጥጥር ስር ማዋሉን አስታውቋል።

የዞኑ ፖሊስ መምሪያ ሃላፊ ረዳት ኮሚሽነር ዶክተር ካሳ እንደተናገሩት በዞኑ እየደረሰ ያለውን የትራፊክ አደጋ ለመከላከልና በትራንስፖርት ዘርፍ የሚስተዋሉ ህገ ወጥ ተግባራትን ለመቆጣጠር ትኩረት ተደርጎ እየተሰራ ነው።

መምሪያው የትራፊክ አደጋን ለመከላከል በአንድ ሳምንት ጊዜ ውስጥ በዞኑ የሚገኙ ትራፊክ ፖሊሶችን በዘመቻ መልክ በማሰማራት ህገወጦችን ለመቆጣጠር በተሰራው ስራ ውጤታማ ተግባር መፈጸሙን ገልጸዋል።

በዘመቻው ያለ ሰሌዳ፣ ያለመንጃ ፍቃድና ትርፍ ሰው በመጫን ሲያሽከረክሩ የነበሩ 273 የባለሁለትና 87 ባለሶስት እግር በጥቅሉ ከ360 በላይ ህገ ወጥ ተሽከርካሪዎችን በቁጥጥር ስር ማድረግ መቻሉን ገልጸዋል።

በተለይም በትራንስፖርት ዘርፍ ላይ ሲስተዋሉ ከነበሩ ችግሮች መካከል ተሽከርካሪዎች ከመናኸሪያ ውጭ ከተቀመጠው የዲጂታል አሰራር ውጪ ተሳፋሪዎችን የመጫን ሁኔታዎች ተጠቃሽ መሆናቸውን ገልጸዋል።

ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት ወንበር ሳይዝ በትርፍነት የሚጫን ማንኛውም ተሳፋሪ ከተሽከርካሪ ወርዶ በእግሩ ወደ መጣበት እንዲመለስ እንደሚደረግ ረዳት ኮሚሽነሩ አሳስበዋል።

ህብረተሰቡም በዞኑ የትራፊክ አደጋን ለመከላከል በሚደረገው ጥረት የመንገድ ግራ መስመር ይዞ በመጓዝ የበኩሉን ድርሻ እንዲወጣ ጥሪ አቅርበዋል።

ዘጋቢ፡ ጦያር ይማም – ከሚዛን ጣቢያችን