በጌዴኦ ዞን እየተሠሩ ያሉ የተለያዩ የልማት ሥራዎች በምክር ቤቱ አባላት ተጎበኙ

በዲላ ዙሪያ ወረዳ በሳይንሳዊ መንገድ እያለሙ በአጭር ጊዜ ምርት የማግኘት ተሞክሮ በሌሎች አካባቢዎች መስፋፋት አንደሚገባው ተጠቁሟል።

በዞኑ በዲላ ዙሪያ ወረዳና በዲላ ከተማ ያሉ የተለያዩ የልማት ሥራዎች በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት አበላት ተጎብኝተዋል።

በመርሃ ግብሩ የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክት ያሰተላለፉት የዲላ ዙሪያ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ታሪኩ ታደሰ በወረዳቸው በሞዴል አርሶ አደሮች ማሳ በክላስተር የለሙ የተለያዩ ሰብሎች የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ አመርቂ ውጤት የተመዘገበበት መሆኑን ለምክር ቤቱ አባላት ገለፃ አደርገውላቸዋል።

የተጎበኙ የአርሶ አደሮች ማሳ በቡና፣ በእንሰትና በሙዝ ክላስተሮች የለሙ ሲሆን ለአብነት ከዚህ ቀደም ከአምስት ዓመት በላይ ጊዜ ይቆይ የነበረው የእንሰት ምርት አሁን ላይ በሳይንሳዊ መንገድ እየለማ በአማካይ ከሁለት ዓመት በታች እየደረሰ መሆኑ ተገልጿል።

ሌላኛው ከተጎበኙ ተቋማት መካከል የዲላ ከተማ እያሰገነባ የሚገኘው ውሃ ማጠራቀሚያ ሪዘርቫየርና የመስመር ዝርጋታ ሥራዎች አሁን ከዘጠና አምሰት በመቶ በላይ መድረሱ የተገለጸ ሲሆን መቶ ሜትር አካባቢ የሚቀረው የመሥመር ዝርጋታ ከተጠናቀቀ እስከ ነሐሴ 30 ድረስ ለአገልግሎት ክፍት ይደረጋል ተብሎ እንደሚጠበቅ ተናግረዋል።

በከተማው እየተከናወኑ ካሉ አራቱ የውሃ ጥልቅ ጉድጓዶች ሁለቱ ሙሉ በሙሉ ተጠናቀው ከዋና መሰመር ጋር የማገናኘት ሥራ በመሠራቱ በከተማው 2 መቶ 12 ኩቢክ ሜትር በሰከንድ ውሃ በማመንጨት በሳምንት አንድ ጊዜ ይሠራጭ የነበረው ውሃ በአንዳንድ አካባቢዎች ላይ በሳምንት ሁለትና ሦስት ጊዜ ማሠራጨት ተጀምሯል ብለዋል።

በመጨረሻም የዞኑ አዲሱ አስተዳደር ህንፃ፣ የመሰብሰቢያ አዳራሽ፣ የሚችሌ ጀግኖች ሐውልት፣ የከተማው እግረኛ መንገድና የኮሪደር ልማት ሥራዎች በምክር ቤቱ አበላት ተጎብተዋል።

የተጎበኙ የልማት ሥራዎች በዞኑ ተሰፋ ሰጪ መሆናቸውን የጠቁመት የምክር ቤቱ አባላት ተሞክሮዎቹ በሁሉም መዋቅሮች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ አሳስበዋል።

ዘጋቢ፡ ተሰፋዬ ጎበና – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን