ዶክተር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ የዳማ ወንዝ ቁጥር 1 ድልድይን መርቀው ከፈቱ

ዶክተር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ የዳማ ወንዝ ቁጥር 1 ድልድይን መርቀው ከፈቱ

ሀዋሳ፡ ሐምሌ 29/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳደር ዶክተር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ የሰሜን ቤንች እና የጊዲ ቤንች ወረዳዎችን የሚያገናኘውን የዳማ ወንዝ ቁጥር 1 ድልድይን መርቀው ለአገለግሎት ክፍት አድረገዋል፡፡

ድልድዩ ከ29 ሚሊየን ብር በላይ በጀት የተገነባ ሲሆን ከዚህ ቀደም ወንዙ የበርካታ ሰዎችን ህይወትና ንብረትን ቀጥፏል፡፡

በዛሬው ዕለት ለምርቃት የበቃው የዳማ ቁጥር 1 ድልድይ በቀድሞ የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦች ክልል መንግስት ግንባታው የተጀመረ ሲሆን በተለያዩ ምክንያቶች ሳይጠናቀቅ የቆየ እንደሆነም ተገልጿል።

በዚህም የበርካታ ሰዎችን ህይወትና ንብረትን ቀጥፎ ከፍተኛ ጉዳት እያስከተለ በመምጣቱ በአዲሱ ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል መንግስት በጀት ትኩረት ተሰጥቶ የተገነባ ሲሆን  የሰሜን ቤንችና ጊዲ ቤንች ወረዳዎችን የሚያገናኝ ድልድይ ነው።

የድልድዩ መመረቅ ለአርሶ አደሩም ሆነ ለአካባቢው ማህበረሰብ ማህበራዊ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ፋይዳ የጎላ እንደሆነም ተመላክቷል።

ድልድዩ 42 ሜትር ርዝመት ያለው ሲሆን ከ29 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ ተጠናቆ ለትራንስፖርት አገለግሎት ክፍት ሆኗል።

የዳማ ቁጥር 1 ድልድይ ግንባታ መሠረተ ድንጋይ በቀድሞ ቤንች ሸኮ ዞን ዋና አስተዳደሪ በነበሩት በአቶ ፍቅሬ አማን ሐምሌ 30/2012 የመሠረተ ድንጋይ መቀመጡ ይታወሳል።

በመርሃ-ግብሩ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳደር ዶክተር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ፣ የመንግስት ዋና ተጠሪና የክልሉ ብልፅግና ቅርንጫፍ ፅፈት ቤት ኃላፊ አቶ ፀጋዬ ማሞ የክልሉ ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ አቶ ወንድሙ ኩርታ ፣የቤንች ሸኮ ዞን ዋና አስተዳደር አቶ ሀብታሙ ካፍቲን የዞኑ የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ደግፌ ኩድን ጨምሮ የክልል ፣ የዞንና የወረዳ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎችን ጨምሮ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተሳትፈዋል።

ዘጋቢ፡ አብዲሳ ዮናስ – ከሚዛን ጣቢያችን