ኢትዮጵያዊያን አትሌቶች ለሜዳልያ የሚጠበቁባቸው ሁለት የፍፃሜ ውድድሮች በዛሬው ዕለት ይካሄዳሉ

ኢትዮጵያዊያን አትሌቶች ለሜዳልያ የሚጠበቁባቸው ሁለት የፍፃሜ ውድድሮች በዛሬው ዕለት ይካሄዳሉ

በ33ኛው የፓሪስ ኦሎምፒክ ኢትዮጵያዊያን አትሌቶች ለሜዳልያው አሸናፊነት የሚጠበቁባቸው የ5 ሺህ እና የ800 ሴቶች የፍፃሜ ውድድሮች ዛሬ ምሽት ይካሄዳሉ።

ሦስት እንስት አትሌቶች ኢትዮጵያን ወክለው የሚወዳደሩበት የሴቶች 5 ሺህ ሜትር የሩጫ ውድድር ምሽት 4 ሰዓት ከ10 ላይ ይካሄዳል።

የርቀቱ የዓለም ክብረወሰን ባለቤቷ አትሌት ጉዳፍ ፀጋዬ፣ አትሌት መዲና ኢሳና አትሌት እጅጋየሁ ታዬ በፍፃሜው የሩጫ ውድድር በኢትዮጵያ በኩል ተወዳዳሪዎች ናቸው።

ምሽት 4 ሰዓት ከ45 ላይ ደግሞ የ800 ሜትር ሴቶች ፍፃሜ የሩጫ ውድድር ይደረጋል።

ሁለት የማጣሪያ ውድድሮችን በአስደናቂ ብቃት በማለፍ ለፍፃሜው መድረስ የቻሉት አትሌት ፅጌ ዱጉማና አትሌት ወርቅነሽ መሰለ በርቀቱ ለኢትዮጵያ በኦሎምፒክ የመጀመሪያውን ሜዳልያ በማስገኘት በታሪክ መዝገብ ለመፃፍ ይሮጣሉ።

ከሁለቱ የፍፃሜ ሩጫ ውድድሮች ቀደም ብሎ ዛሬ ምሽት 2 ሰዓት ከ04 ላይ የወንዶች 3 ሺህ ሜትር መሰናክል የማጣሪያ ውድድር ይካሄዳል።

በማጣሪያው የርቀቱ የዓለም ክብረወሰን ባለቤት የሆነው አትሌት ለሜቻ ግርማ፣ አትሌት ጌትነት ዋለና አትሌት ሳሙኤል ፍሬው ወደ ፍፃሜው ለማለፍ ይወዳደራሉ።

ዘጋቢ፡ ሙሉቀን ባሳ