ይህ የተገለጸው የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ እና የኢትዮጵያ ብሔራዊ የቡና ማህበር በጋራ በመተባበር የክልሉን የቡና ልማትና ግብይት ተግባራትን ለማዘመን በተደረገው ምክክር ላይ ነው።
በቡና አቅርቦትና ግብይት ላይ የሚስተዋሉ ችግሮች ከወረዳ እስከ ክልል ያሉ ባለድርሻ ተቋማት ባለመናበብ ህገወጥ ሥራዎች ነበሩ ያሉት የኢትዮጵያ ብሔራዊ የቡና ማህበር ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሁሴን አምቦ፤ የመንግስት መዋቅር ከላይ እስከታች ችግሩን ለመፍታት ከሚመለከታቸው ጋር በጋራ መሠራት እንዳለበት መወያየታቸውን ተናግረዋል።
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በ2017 ዓ.ም በቡና አቅርቦት ከኦሮሚያ ቀጥሎ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ በክልሉ ያሉ ዞኖች ውስጥ ከቡና ሽፋንና አቅርቦት ጋር ያለው ህገወጥ ንግድ ችግር በጋራ መፍታት ይገባል ሲሉ አስገንዝበዋል።
የቡና ምርትና ጥራት የሚጨምርበትና ህገወጦች ተወግደው ህጋዊ የንግድ ግብይት እንዲኖር መሥራት ይገባል ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ ከፌደራል እስከ ወረዳ አስተዳደርና የግሉ ሴክተር በጋራ በመቀናጀት ቡና የሚገባውን ከፍታ እንዲያገኝ ማድረግ ይኖርብናል ብለዋል።
ክልሉ ለማዕከላዊ ገበያ ካቀረበው 46 ሺህ ቶን ቡና 40 ሺህ ቶኑ ከጌዴኦ የተላከ ነው ያሉት የጌዴኦ ዞን ቡናና ቅመማቅመም ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ አማኑኤል ወርቁ፤ በጋራ ተቀናጅቶ መሥራት ምርታማነትን የሚጨምሩ ፓኬጆች ላይ ትኩረት መደረጉ ለዚህ ስኬት እንዳበቃቸው ገልጸዋል። ይህም የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ለማሳደግ ያለው ድርሻ ከፍተኛ መሆኑን በመጠቆም፡፡
በወላይታ ዞን 42 ሺህ ሄክታር የቡና እርሻ ቢኖርም ለማዕከላዊ ገበያ ከሁለት ሺህ ቶን በላይ ማቅረብ እንዳልተቻለና ለዚህም ምክንያት ያሉትን የወላይታ ዞን ቡናና ቅመማቅመም ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ደመቀ ኩኬ የኮንትሮባንድ ንግድ ተጠቃሽ መሆኑን ጠቁመዋል።
ዘጋቢ: ውብሸት ካሣሁን – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን

More Stories
6ኛው ሀገር አቀፍ የሀይማኖት ተቋማት ጉባኤ የሰላም ኮንፍረንስ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በሆሳዕና ከተማ በተለያዩ ዝግጅቶች በአብዮ ኤርሳሞ መታሰቢያ ስታዲየም እየተካሄደ ነው
የቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች መንግስት በከተማና በገጠር ለጀመራቸው የልማት እንቅስቃሴዎች ዋነኛ ሞተሮች ናቸው – አበባየሁ ታደሰ (ዶ/ር)
የማህበረሰብ አቀፍ ጤና መድህን አባል በመሆናቸው ከድንገተኛ ህክምና ወጪ እንደታደጋቸው የይርጋጨፌ ወረዳ ነዋሪዎች ገለጹ