ወርልድ ብራይት ኮሌጅ ቡታጅራ ካምፓስ ከዲፕሎማ እስከ ማስተርስ ፕሮግራም በተለያዩ የትምህርት መስኮች ያሰለጠናቸውን 388 ተማሪዎችን አስመረቀ

ወርልድ ብራይት ኮሌጅ ቡታጅራ ካምፓስ ከዲፕሎማ እስከ ማስተርስ ፕሮግራም በተለያዩ የትምህርት መስኮች ያሰለጠናቸውን 388 ተማሪዎችን አስመረቀ

ኮሌጁ በፈረንጆቹ 2030 በምስራቅ አፍሪካ የልህቀት ማዕከልና ግንባር ቀደም የምርምር ተቋም ለመሆን በትኩረት እየሰራ መሆኑም ተጠቁሟል።

የወርልድ ብራይት ኮሌጅ ፕሬዝዳንት ተሰማ አበራ (ዶ/ር) በምረቃ ፕሮግራሙ እንደገለጹት ኮሌጁ ከተመሠረተበት ከ2010 ዓ.ም ጀምሮ ለማህበረሰቡ ትምህርትን ተደራሽ በማድረግ ረገድ በርካታ ተግባራትን ሲያከናውን ቆይቷል::

ኮሌጁ በሰባት ካምፖሶች በ5 ፋካሊቲ ተማሪዎችን በ24 የተለያዩ የትምህርት መስኮች እያሰለጠነ ብቁ፣ ተወዳዳሪ፣ ሀገር ወዳድ ዜጎችን በማፍራት ሀገራዊ ኃላፊነትን በተገቢው እየተወጣ እንደሆነ ዶክተር ተሰማ አመላክተዋል።

ኮሌጁ በፈረንጆቹ 2030 በምስራቅ አፍሪካ የልህቀት ማዕከልና ግንባር ቀደም የምርምር ተቋም ለመሆን በትኩረት እየሰራ መሆኑንም ፕሬዚዳንቱ አስረድተዋል።

በምረቃ መርሃ ግብሩ በክብር እንግድነት የተገኙት በየካቲት ሆስፒታል የውስጥ ደዌ ስፔሻሊስትና ተማራማሪ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ሜዲካል ዳይሬክተር ረዳት ፕሮፌሰር ታሪኩ ፈቃዱ እንዳሉት ሀገራችን የተማረ የሰው ኃይል በሚፈለገው ልክ ስላልደረሰ ወርልድ ብራይት ኮሌጅ ትምህርትን ለዜጎች ተደራሽ በማድረግ እያደረገ ያለው አስተዋጽኦ የጎላ ነው።

ኮሌጁ ከመማር ማስተማርና ከምርምር ስራው ባሻገር ሀገርንና ማህበረሰብን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ተግባራት ላይ የድርሻውን እየተወጣ መሆኑን ረዳት ፕሮፌሰር ታሪኩ ገልጸዋል::

በመርሃ-ግብሩ የተሳተፉት የምስራቅ ጉራጌ ዞን የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና መምሪያ ኃላፍ አቶ ነጋልኝ ዓለሙ በበኩላቸው የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በሀገር ግንባታ ላይ በመሳተፍ እያደረጉት ያለው አስተዋጽኦ የጎላ ነው ብለዋል::

ተመራቂዎች በኮሌጅ ቆይታቸው ያገኙትን ዕውቀት በመጠቀም በስራ ላይ ውጤታማ ለመሆን መትጋት እንዳለባቸውም ኃላፊው መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።

አንዳንድ ያነጋገርናቸው ተመራቂ ተማሪዎች ከኮሌጁ ያገኙትን እውቀት በመጠቀም ስራ ጠባቂ ሳይሆኑ ስራ ፈጣሪዎች በመሆን ለሌሎችም የስራ ዕድል ለመፍጠር እንደሚተጉ ተናግረዋል።

ዘጋቢ: ትዕግስት ተሾመ – ከወልቂጤ ጣቢያችን