በጉራጌ ዞን እዣ ወረዳ በአምበሊ ቀበሌ በህብረተሰብና በመንግስት ትብብር ከ21 ሚሊዮን ብር በላይ የተገነባው የ20 ኪሎ ሜትር የጠጠር መንገድ ተመረቀ

የኢፌዲሪ ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ዶክተር መኩሪያ ኃይሌ እንደገለጹት የጉራጌ ባለሀብቶች የቀድሞ አባቶች አርአያነት ያለውን ተግባር ወጣቱ ትውልድ ማስቀጠል ይኖርበታል።

የተገነባው መንገድ ለረዥም አመታት አገልግሎት መስጠት እንዲችል ህብረተሰቡ መንከባከብና መጠበቅ እንዳለበት አንስተዋል ዶክተር መኩሪያ።

የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ላጫ ጋሩማ እንደአሉት የመንገድን ሁለንተናዊ ጥቅም አስቀድመው የተረዱት የቀድሞ አባቶች ያከናወኑትን አርአያነት ያለው ተግባር አሁን ላይ የዞኑ ባለሀብቶች ተግባሩን እያስቀጠሉት ይገኛሉ።

የመንግስት አቅም ውስን ነው ያሉት አቶ ላጫ በተጠናቀቀው በጀት አመት በዞኑ በርካታ ኪሎ ሜትር መንገድ በማህበረሰቡ ተሳትፎ መሰራቱን ገልጸዋል።

በእዣ ወረዳ የአምበሊ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ደረጃን ለማሻሻልና የመምህራን መኖሪያ ለመገንባት የተጀመረውን ስራ በአጭር ጊዜ ለማጠናቀቅ ሁሉም ርብርብ ማድረግ ይኖርበታል ብለዋል ዋና አስተዳዳሪው።

የጉራጌ ዞን ትራንስፖርትና መንገድ መምሪያ ኃላፊ አቶ ሙራድ ከድር፤ በዞኑ በተጠናቀቀው በጀት አመት 2 መቶ 77 ነጥብ 3 ሚሊዮን ብር በማሰባሰብ 2 መቶ 98 ኪሎ ሜትር መንገድ ተሰርቷል።

የአፈር ስራ ከመስራት ባለፈ 243 ኪሎ ሜትር ጠጠር የማልበስ ስራ፣ ከ104 በላይ የተለያዩ ስትራክቸሮች፣ ድልድዮችንና ቱቦዎችን በመስራት ለትራፊክ ክፍት መደረጉን ተናግረዋል አቶ ሙራድ።

የእዣ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዘውዱ ዱላ በበኩላቸው ቀበሌው በማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማቶች ግንባር ቀደም መሆኑን ጠቅሰው በቀበሌው የመንገድ ችግር መቀረፉ አርሶአደሩ ምርቱን ወደ ገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ ያደርገዋል ብለዋል።

በተያያዘ የአንበሊ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ደረጃውን ለማሻሻል የመሰረት ድንጋይ መጣሉ በቀጣይ ውጤታማ ስራ ለመስራት ይበል የሚያሰኝ ነው ብለዋል ዋና አስተዳዳሪው።

የአካባቢው የልማት ማህበር ኮሚቴ አስተባባሪ አትሌት ተሰማ አብሽሮ፤ ልማት ማህበሩ የአካባቢውን ማህበረሰብ በማስተባበር ከ21 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ በማድረግ 13 ነጥብ 5 ኪሎ ሜትር አዲስና 6 ነጥብ 5 ኪሎ ሜትር ጥገና በማድረግ መንገዱ ተመርቆ ለትራፊክ ክፍት መሆኑን አስረድተዋል።

የቀበሌው ነዋሪ አቶ ተክሉ ቃሩ፣ መቻል ግርማና ታደሰ ዝርጓ የመንገዱ መገንባት ብዙ ችግሮቻቸውን እንደሚቀርፍ በመጠቆም ተሰርቶ ለዚህ በመብቃቱ መደሠታቸውን ገልፀው በቀጣይ የመንገዱን ደህንነት ለመጠበቅ ሁሉም የማህበረሰብ ክፍል የድርሻው እንዲወጣ ጠይቀዋል።

በምረቃ ስነ-ስርዓቱ የኢፌዲሪ ሲቭል ሰርቪስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ዶ/ር መኩሪያ ኃይሌ፣ የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ላጫ ጋሩማ፣ የዞኑ ዋና አፈ-ጉባኤ ወይዘሮ ልክነሽ ስርገማ፣ የዞኑ የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ክብሩ ፈቀደ እና የወረዳው ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዘውዱ ዱላን ጨምሮ የዞንና የወረዳው የስራ ኃላፊዎችና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እነግዶች ተገኝተዋል።

ዘጋቢ፡ ዝናሽ ሙሉጌታ – ከወልቂጤ ጣቢያችን