11ኛ ቅርንጫፍ ሆኖ የተመሠረተው የደቡብ ሬዲዮና ቴሌቭዥን ድርጅት ማሻ ኤፍ ኤም 103.8 የሬዲዮ ጣቢያ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳደር ዶ/ር ኢንጂነር ኔጋሽ ዋጌሾ ተመረቀ

በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ ርዕሰ መስተዳድር ዶክተር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ ባደረጉት ንግግር በክልሉና በዞኑ አስተዳደር ወደስራ የገባው የሬዲዮ ጣቢያው የህዝቡን የመልካም አስተዳደር ጥያቄ የመለሰ ነው ብለዋል።

የማሻ ኤፍ ኤም 103.8 ከማዝናናትና መረጃ ከመስጠት በተጨማሪ አካባቢው ታሪካዊ፣ ባህላዊ፣ የሚማርኩ መልክዓ ምድርና የመስህቦች ባለቤት በመሆኑ ለአለም ማስተዋወቅ እንደሚገባውም አንስተዋል።

ክልሉ ሚዲያ ኔትወርክ በማደራጀት ወደስራ የማስገባት ሂደት ላይ እንደሚገኝም ርዕሰ መስተዳድሩ ተናግረዋል፡፡

የክልሉ መንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ፀጋዬ ማሞ በበኩላቸው የህዝብን የሰላም፣ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች እንዲረጋገጡ አዳዲስ ሀሳቦችን በማፍለቅ የሬዲዮ ጣቢያው ለህብረተሰቡ ተስፋ ሊሆን ይገባል ብለዋል፡፡

በምረቃው ፕሮግራሙ ላይ የክልሉ ምክር ቤት ዋና አፌ ጉባኤ አቶ ወንድሙ ኩርታ እና ሌሎች የፌደራል፣ የክልል፣ የሸካ ባህላዊ አስተዳደር፣ የዞን፣ የወረዳና የከተማ አስተዳደር አመራሮችና ባለድርሻ ተገኝተዋል።

ዘጋቢ፡ ልጃለም ማሞ – ከማሻ ጣቢያችን