እንደ ሀገር የተያዘውን የወባ በሽታ መከላከል ሥራ ውጤታማ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታወቀ

በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በደቡብ ኦሞ ዞን ወባን ለመከላከል በሚያስችሉ ጉዳዮች ዙሪያ ለባለድርሻ አካላት በኛንጋቶም ወረዳ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ሰልጠና ሰጥቷል።

የኛንጋቶም ወረዳ ጤና ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ሎላር ኤኬኖ፤ በሽታን መከላከልና አክሞ ማዳንን መሠረት ያደረገውን የጤና ፖሊስ መሠረት በማድረግ የወባ በሽታን የግልና የአካባቢ ንፅህናን በመጠበቅ ብቻ መከላከል የምንችለው በመሆኑ ይህንን ለማጠናከር የጤና ኤክስቴንሽን እና ሌሎች ባለሙያዎችን በማሰልጠን ወደ ተግባር እንደሚገባ ተናግረዋል።

የኛንጋቶም ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪና መስኖና ቆላማ አካባቢ ልማት ጽ/ቤት ኃላፊ ኢንጂነር ሎካሎቦንግ ሎስኮና ከበሽታ መከላከል ሥራዎች አንዱ የወባ በሽታን መከላከል በመሆኑ እንደ ወረዳችን የጤና ኤክስቴንሽንና ሌሎች የጤና ባለሙያዎች ባደረጉት የተቀናጀ ጥረት ለመጣው ውጤት አመስግነው፤ በአጎበር ስርጭት የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎችን በማስፋት ሊሰራ እንደሚገባ አሳስበዋል።

በዘንድሮ ዓመት በዞኑ ካሉ ወረዳዎች የኛንጋቶም ወረዳ በወባ ስርጭት የተሻለ አፈፃፀም ማከናወኑን ያስታወሱት ምክትል አስተዳዳሪው ወቅቱ የዝናብ ወቅት እንደመሆኑ የአጎበር ስርጭቱን በፍትሐዊነት ማዳረስ እንደሚገባ ገልፀዋል።

በጠቅላይ ሚኒስቴር ጽ/ቤት የማላሪያ ኢንሼቲቭ ሱፐርቫይዘር አቶ ናደው ዱከሌ እንደ ሀገር እየተከሰቱ ያሉ የወባ በሽታ ጫናዎችን ለመከላከል ባለፉት ዓመታት የስልጠናና ሌሎች ሥራዎች በውጤታማነት መከናወናቸውን አስታውሰዋል።

አክለውም በክልሉ የኬምካል ርጭት፣ የአጎበር እደላ፣ የአካባቢ ንፅህናና የህክምና አገልግሎቶች በአግባቡ እንዲሰጡ ለማስቻል ታስቦ እየተሠራ መሆኑንና የዚህ አካል ለሆኑ የጤና ኤክስቴንሽና ባለሙያዎች ሰልጠና መሰጠቱን ተናግረዋል።

የስልጠናው ተሳታፊ የጤና ኤክስቴንሽንና ሌሎች የጤና ባለሙያዎች በበኩላቸው ስልጠናው አራቱን የጤና ተግባራት በአግባቡ በመገንዘብ እንድናስገነዝብ አቅም የፈጠረ ስልጠና መሆኑን ተናግረዋል።

ዘጋቢ: ከተማ በየነ – ከጂንካ ጣቢያችን