የደቡብ ኦሞ ዞን ምክር ቤት የ2017 ዓ/ም ማስፈፀሚያ 1 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር በላይ አፀደቀ

ሀዋሳ፡ ሐምሌ 24/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) ምክር ቤቱ 4ኛ ዙር 11ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 3ኛ መደበኛ ጉባኤ የ2017 ዓ/ም የዞኑ ማስፈፀሚያ በጀት 1 ቢሊዮን 496 ሚሊዮን 511 ሺህ ብር አድርጎ አጽድቋል።

ውስን የሆነውን የመንግስትና የህዝብ ሀብት የልማትና መልካም አስተዳደር ችግሮችን መፍታት በሚያስችል መልኩ ተፈፃሚ መሆን እንዳለበት የደቡብ ኦሞ ዞን ምክር ቤት ዋና አፈጉባኤ አቶ ሎስንዴ ሎኛሱዋ አሳስበዋል።

የህዝቡ አዳጊ ፍላጎቶች ከመቼውም ጊዜ በላይ እየጨመረ የመጣ በመሆኑ የፀደቀው በጀት ሳይባክን ለታለመለት ዓላማ እንዲውል በልዩ ጥንቃቄ ሊመራ እንደሚገባ የምክር ቤት አባላት በሰጡት አስተያየት ተናግረዋል።

ከዚህ በተጨማሪ የዞኑ ከፍተኛ ፍርድ ቤት የ2016 ዓ/ም ዕቅድ አፈፃፀምና የ2017 ጠቋሚ ዕቅድ ቀርቦ ዝርዝር ውይይት የተካሄደበት ሲሆን፥ በተለይ ፍርድ ቤቶች ገለልተኛ ሆነው ህዝቡን በግልፀኝነት ማገልገል እንዳለባቸው ተጠይቋል።

ምክር ቤቱ የቋሚ ኮሚቴ አባላትን የሰየመ ሲሆን፥ ለስድስት የዞን መምሪያ ኃላፊዎች፣ የቱርሚ ከተማ አስተዳደር እና የዳሰነች ወረዳ ፍርድ ቤቶች ፕሬዝዳቶች ሹመትም በምክር ቤቱ አባላት ቀርቦ በሙሉ ድምፅ ፀድቋል።

ዘጋቢ: ተመስገን አበራ – ከጂንካ ጣቢያችን