በ2016 ዓ.ም በሁሉም ዘርፍ ውጤታማ ስራዎች ቢሰሩም በቀጣይ ክፍተቶችን ለማረም የጋራ ጥረት እንደሚጠይቅ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው ገለፁ

ለመገናኛ ብዙሀን በወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ መግለጫ የሰጡት ርዕሰ መስተዳድሩ ክልሉ ከተመሰረተ በኋላ 7 ማዕከላትን በማዋቀር በሁሉም ማዕከላት ሰራተኞችን መመደብና ማጓጓዝ እንዲሁም እቅዶችን ነድፎ ወደ ስራ መግባት በዝግጅት ምዕራፍ በጠንካራ ጎን የታየ መሆኑን አንስተዋል።

ወደ ትግበራ ምዕራፍ ሲገባ የነበሩ የአደረጃጀት ጥያቄዎች፣ ሀሰተኛ ማህበራዊ ሚዲያዎች፣ ደመወዝ የመክፈል ችግር፣ ህገወጥ የንግድ ስርዐትና መሰል የፀጥታ ሁኔታዎች ተግዳሮት ቢፈጥሩም በተወሰደው የእርምት እርምጃ ለውጦች ተመዝግበዋል ብለዋል።

ክልሉ የነበረበት ውዝፍ እዳ እንከን የፈጠረ ቢሆንም ባለፈው በጀት አመት 3 ቢሊዮን ብር ወይም የእዳውን 60 በመቶ በመክፈል ዘርፈ ብዙ የበጀት ችግሮችን ለመፍታት ተሞክሯል።

በበጀት ዓመቱ ትኩረት የሚሹ እንደ ፀጥታ፣ ግብርና፣ ገቢ፣ ትምህርት፣ ጤና፣ ንግድ፣ ኢንቨስትመንትና የስራ ዕድል ፈጠራ ስራዎችን በመለየት በተሰራው ስራ ለውጥ ተመዝግቧል ሲሉ አክለዋል።

አመራሩ በቀጣይ አመት የተሻሉ ለውጦችን ለማምጣት የተሰጠን ስራ ቆጥሮ መስራት ላይ እንዲያተኩር ይደረጋል ሲሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው አመላክተዋል።

በ2017 በጀት ዓመት ሰላምን ማረጋገጥ፣ ምርታማነት ማሳደግ፣ የህብረተሰቡን ኑሮ ማረጋጋትና የህዝብን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ የርብርብ ተግባራት ይሆናሉ ብለዋል።

ዘጋቢ፡ ባዬ በልስቲ