በመኸር የመስኖ እርሻ ሥራ የአርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት እንደሚሠራ ተገለጸ

በመኸር የመስኖ እርሻ ሥራ የአርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት እንደሚሠራ ተገለጸ

ሀዋሳ፡ ሐምሌ 24/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በመኸር የመስኖ እርሻ ሥራ የአርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት እንደሚሠራ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መስኖና ቆላማ አከባቢ ልማት ቢሮ ገለፀ፡፡

ቢሮው በደቡብ ኦሞ ዞን ኛንጋቶምና ዳሰነች ወረዳ ተገኝተው የመኸር እርሻ ዝግጅትና የመስኖ ተቋማት ነባራዊ ሁኔታን ተመልክተዋል፡፡

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መስኖና ቆላማ አከባቢ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ታረቀኝ ሀብቴ በደቡብ ኦሞ ዞን ዳሰነችና ኛንጋቶም ወረዳ በመስኖ የሚለሙ ማሳዎችን ያሉበትን ዝግጅት መመልከታቸውን ጠቁመው፥ በአከባቢው ያለውን እምቅ ፀጋ በመጠቀም የተሻለ ምርት ለማግኘት የጋራ ርብርብ ይደረጋል ብለዋል፡፡

የአርብቶ አደሩን የምግብ ዋስትና በማረጋገጥና ውሃን ማዕከል ያደረገ የመንደር ማሰባሰብ ሥራ ማጠናከር እንደሚያስፈልግ አቶ ታረቀኝ ሀብቴ ገልፀዋል፡፡

በክልሉ መስኖና ቆላማ አከባቢ ልማት ቢሮ የአርብቶ አደር አከባቢ ልዩ ድጋፍና የመሠረተ ልማት አስተባባሪ አቶ አይዴ ሎሞዶ እንደገለፁት አርብቶ አደሩን ከተረጅነት ለማላቀቅ የቴክኖሎጂ አቅርቦትን በማሳደግ በ2017 በጀት አመት ከ19 ሺህ 400 በላይ ሄክታር መሬት በማልማት ከ80 ሺህ 800 በላይ የማህበረሰብ ክፍልን ተጠቃሚ ለማድረግ ታቅዶ እየተሠራ መሆኑን ገልፀዋል፡፡

አክለውም ክልሉ በመኸር እርሻ ለማልማት ካቀደው 3 ሺህ 575 ሄክታር መሬት በሜካናይዘሽን እርሻ የታገዘ 2 ሺህ 350 ሄክታር መሬት ዝግጅት መጠናቀቁን አስረድተዋል፡፡

ዘጋቢ፡ ተመስገን አሰፋ – ከጂንካ ጣቢያችን