ስማርት ሲቲ፣ ኮርደር ልማትና የፅዳትና ውበት ሥራዎች በበጀት አመቱ ተጠናክረው ይቀጥላሉ – ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው

ሀዋሳ፡ ሀምሌ 18/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በክልሉ የስማርት ሲቲ፣ ኮርደር ልማትና የፅዳትና ውበት ሥራዎች በበጀት አመቱ ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው ገልፀዋል።

ርዕሰ መስተዳድሩ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እያካሄደ ባለው 6ኛ ዙር 4ኛ አመት የሥራ ዘመን 2ኛ መደበኛ ጉባኤ ላይ ተገኝተው በ2017 በጀት አመት ጠቋሚ እቅድ አቅርበዋል።

በክልሉ ሁለት ከተሞችን ወደ ስማርት ሲቲ ለማሳደግ ጥናቶች መካሄዳቸውን የገለፁት ርዕሰ መስተዳድሩ ለዚህም የሆሳዕናና ቡታጅራ ከተሞች መለየታቸውን ተናግረዋል።

በ10 ከተሞች ላይ የተሟላ አገልግሎት የሚሠጥ የመፀዳ ቤት እንደሚገነባም ገልፀዋል።

የኮሪደር ልማት በሆሳዕና ከተማ የተጀመረ ሲሆን ቡታጅራና ወወራቤ ከተሞችም በተጨማሪነት የተለዩ መሆናቸውን አብራርተዋል።

በፕሮጀክት ረገድ የተሣኩና ያልተሣኩ መኖራቸውን አንስተው ያልተሳኩት ላይ የቅርብ ክትትል በማድረግ ለማጠናቀቅ እንሠራለን ብለዋል።

የሠላምና ፀጥታ፣ ምርታማነትን መጨመር፣ ክልሉ ማመንጨት በሚችለው ልክ ገቢ መሠብሠብ፣ ሥራ ዕድል ፈጠራ፣ ጤና፣ ትምህርት እንዲሁም መሠረተ ልማት ላይ ያተኮሩ የክልሉን አጠቃላይ የበጀት አመቱን እቅድ አቅርበው በአባላቱ ውይይት ተደርጎበታል።

በአባላቱ ውይይት የተደረገበትን የክልሉ 2017 በጀት አመት ጠቋሚ እቅድ ምክር ቤቱ በሙሉ ድምፅ አፅድቋል።

ዘጋቢ፡ ማሬ ቃጦ