በበልግ ሥራ በተቀናጀ መልኩ በተከናወኑ ተግባራት የተሻለ ውጤት መመዘገቡ ተገለጸ

በበልግ ሥራ በተቀናጀ መልኩ በተከናወኑ ተግባራት የተሻለ ውጤት መመዘገቡ ተገለጸ

ሀዋሳ፡ ሐምሌ 17/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በበጋ መስኖና በበልግ ሥራ በተቀናጀ መልኩ በተከናወኑ ተግባራት የተሻለ ውጤት መመዘገቡን በጌዴኦ ዞን የጮርሶ ወረዳ አስተዳደር አስታወቀ።

በበልጉ የነበረውን ምርጥ ተሞክሮ በመቀመር ለመኸር እርሻ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች በመጠናቀቅ ላይ እንደሚገኝ ተገልጿል፡፡

በወረዳው የ2016 ዓ/ም የሥራ አፈፃፀምና የ2016/17 ዓ/ም የመኸር እርሻ የሥራ ዕቅድ ሪፖርት ቀርቦ ውይይት ተካህዷል፡፡

የጮርሶ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አየለ ደያሶ በባለፈው ዓመት በበጋ መስኖ በስንዴ፣ በድንችና በሌሎች ዘርፎች እንዲሁም በበልግ ግብርና በተከናወኑ ተግባራት የተሻለ ውጤት መመዝገቡን ተናግረዋል፡፡

የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የእንስሳትን አቅም ለማጠናከር በአዳዲስ መሬትና የመተካት ሥራዎች በስፋት መከናወናቸውን ገልፀው በዚህም ከ8 ሚሊዮን በላይ የእንሰት ችግኞች መተከላቸውን አስረድተዋል፡፡

በበጋ መስኖ ሥራና በበልግ እርሻ የነበረውን ድክመት በመቅረፍ የነበረውን ጥንካሬ ይበልጥ በማጎልበት፣ ምርጥ ተሞክሮዎችን በመቀመርና ተግባር ላይ በማዋል በመኸር እርሻ የተሻለ ምርት ለመሰበሰብ በትኩረት ለመፈፀም መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል፡፡

የወረዳው ግብርና ልማት ጽ/ቤት ምክትልና የእርሻ ዘርፍ ኃላፊ አቶ እንደልቡ በራሶ የአፈፃፀምና የዕቅድ ሪፖርት ባቀረቡበት ወቅት ወረዳው በደጋ አየር ንብረት የሚመደብ በመሆኑና የተለያዩ የውሃ አማራጮች ያለበት በመሆኑ በበጋ መስኖ ድንች፣ በቆሎ፣ ስንዴ፣ ገብስና የመሳሰሉ ሰብሎችን በማምረት ጥሩ ውጤት ማስመዘገባቸውን ገልጸዋል፡፡

በወረዳው በአንዳንድ ቀበሌዎችና በሞዴል አርሶአደሮች የተገኙ ምርጥ ተሞክሮዎችን በመቀመር ለሌሎች ለማስፋፋት እየተሠራ እንደሆነም አብራርተዋል፡፡

በ2016/17 ዓ/ም መኸር እርሻ በዋና ዋና ሰብልና በሌሎች ሰብሎች ከአራት ሺህ ሄክታር መሬት በላይ ለማልማት ታቅዶ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች በመጠናቀቅ ላይ እንደሚገኙ ኃላፊው በሪፖርታቸው አመላክተዋል፡፡

በወይይት መድረኩ የወረዳው አመራሮች፣ የዘርፉ ባለሙያዎችና የቀበሌ መዋቅሮች ተሳትፈዋል፡፡

ዘጋቢ፡ እምነት ሽፈራው – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን