የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል ቡና ሻይና ቅመማ ቅመም ባለስልጣን ለዞን፣ ለወረዳና ለቀበሌ ባለሙያዎች የአሰልጣኞች ስልጠና በሚዛን አማን ከተማ እየሰጠ ነው

የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል ቡና ሻይና ቅመማ ቅመም ባለስልጣን በዋና ዋና የቅመማ ቅመም ሰብሎች አመራረት፣ አዘገጃጀትና እሴት ጭመራ ላይ ለዞን፣ ለወረዳ እና ለቀበሌ ባለሙያዎች የአሰልጣኞች ስልጠና በሚዛን አማን ከተማ እየተሰጠ ነው።

በስልጠናው የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክት ያስተላለፉት በቤንች ሸኮ ዞን ግብርና አካባቢ ጥበቃ ህብረት ስራ መምሪያ ምክትል ኃላፊና የቡና፣ ሻይና ቅመማ ቅመም ዘርፍ ኃላፊ ወይዘሪት ወርቅነሽ ባድንስ እንደገለፁት ክልሉ የግብርና ኤክስፖርት ምርቶች በከፍተኛ ደረጃ በጥራትና በብዛት እያመረተ የሚገኝ አካባቢ ነው።

የኤክስፖርት ምረቶቹ በአመራረት፣ አዘገጃጀትና በእሴት ጭመራ ከፍተኛውን የኢኮኖሚ ገቢ እና ዶላር እንዲያመነጭ ያስችል ዘንድ ባለስልጣኑ ያዘጋጀውን ስልጠና ተሳታፊዎቹ በትኩረት ሊከታተሉ እንደሚገባም አስገንዝበዋል።

የክልሉ የቡና፣ ሻይና ቅመማ ቅመም ባለስልጣን ምክትል ዳይሬክተር አቶ በላይ ኮጀኣብ በበኩላቸው ክልሉ 92 ሺህ ሄክታር መሬት ሽፋን የቅመማ ቅመም ምረት ከመኖሩም ባለፈ በሶስቱም ዘርፎች ቡና፣ ሻይና ቅመማ ቅመምን በማቀናጀት እየተሰራ ይገኛል ብለዋል።

ዘርፉ በበቂ ሁኔታ ያልተሰራበት በመሆኑ በምርታማነት፣ በግብይትና በአዘገጃጀት ላይ ያሉት ችግሮችን ለመፍታት እየተሰጠ ያለውን የአሰልጣኞች ስልጠና እስከ ቀበሌ ድረስ ያሉ ባለሙያዎች ጋር ተቀናጅተው መሥራት ስላለባቸው በትኩረት እንዲከታተሉት አፅንኦት ሰጥተዋል።

በስልጠናው የክልሉ የቡና፣ ሻይና ቅመማ ቅመም ባለስልጣን ምክትል ዳይሬክተሩ አቶ በላይ ኮጀኣብ እና በቤንች ሸኮ ዞን ግብርና፣ አካባቢ ጥበቃና ህብረት ስራ መምሪያ ምክትል ኃላፊ እና የቡና ሻይና ቅመማ ቅመም ዘርፍ ኃላፊ ወይዘሪት ወርቅነሽ ባድንስን ጨምሮ የዞን፣ የወረዳና የቀበሌ የዘርፉ ባለሙያዎች እየተሳተፉ ይገኛሉ።

ዘጋቢ፡ አብዲሳ ዮናስ – ከሚዛን ጣቢያችን