ሰው ሰራሽ አስተውሎት

ሰው ሰራሽ አስተውሎት

በደረጀ ጥላሁን

አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ (ሰው ሰራሽ አስተውሎት) ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የሰው ልጆችን ህይወት በብዙ መልኩ እያቀለለው ይገኛል። የሰው ሰራሽ አስተውሎት በኢንዱስትሪዎች እና በተለያዩ የሥራ ዘርፎች ላይ በብዛት እየተስተዋለ ሲሆን ይህም የምንኖርበትን እና የምንሰራበትን መንገድ የተሻለ እንዲሆን ያደርገዋል።

አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ አሰልቺ እና ተደጋጋሚ ስራዎችን አውቶሜትድ በሆነ መልኩ ያዘጋጃል። ለምሳሌ ለኩባንያዎች የደንበኞችን ፍላጎትና ጥያቄዎችን የመመለስ ስራን በመሸፈን የሰው ኃይል ወደ ሌሎች የስራ ዘርፎች እንዲሰማሩ ማስቻሉ ነው። በተመሳሳይ በማምረቻው ዘርፍ ሮቦቶች ለሰው ልጆች ፈታኝ እና አደገኛ የሆኑ የስራ ዘርፎችን እንዲሸፍኑ በማድረግ ምርታማነት እንዲጨምር እያደረጉ መሆኑን ነው መረጃዎች የሚያሳዩት።

በግብርናው መስክ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ የሰብል ምርትን ለማሳደግ እና ብክነትን ለመቀነስ ጥቅም ላይ ይውላል። በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ የጎለበተ መሳሪያ የአፈርን እርጥበት ደረጃ፣ የሙቀት መጠን እና ሌሎች የአካባቢ ሁኔታዎችን በመከታተል አርሶ አደሮች ለመዝራት እና ለማጨድ መረጃ ላይ የተመሰረተ ውሳኔ እንዲወስኑ የሚያግዝ እውነተኛ መረጃን ያቀርባል። እንዲሁም ፀረ-ተባይ እና ሌሎች ጎጂ ኬሚካሎች አጠቃቀምን የሚቀንሱ ትክክለኛ የእርሻ ዘዴዎችን ለማዘጋጀት ጥቅም ላይ ይውላል።

አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ የዓለም አንገብጋቢ ፈተናዎችን ለመፍታት ጥቅም ላይ ይውላል። የአየር ንብረት ለውጥን በመዋጋት፣ የአየር ሁኔታን ለመተንበይ እና ከአየር ንብረት ጋር በተያያዙ ክስተቶች ለጎርፍ እና ድርቅ የተጋለጡ አካባቢዎችን ለመለየት እንዲሁም ሞዴሎችን ለማዘጋጀት ያገለግላል፡፡ በተጨማሪም አዳዲስ ኃይል ቆጣቢ ቴክኖሎጂዎችን ለማዳበር እና የኢንዱስትሪዎችን የካርቦን መጠን ለመቀነስ ይጠቅማል፡፡

ሰው ሰራሽ አስተውሎት የተለያዩ የገሃዱ ዓለም ችግሮችን ለመፍታት ቴክኒኮችን በማዘጋጀት ረገድ ስኬታማ ሊሆን ይችላል። ለምሳሌ የትራፊክ ምልክቶችን በወቅቱ ማስተካከል እና የትራፊክ መጨናነቅን ለመቆጣጠር እንዲሁም የህክምና ባለሙያዎች ምርመራ ሲያደርጉ ምስሎችን እንዲመረምሩ ይረዳል። በተጨማሪም ተሽከርካሪዎቹ አካባቢያቸውን እንዲረዱ የእይታ መረጃዎችን በማቀናበር በራስ የሚነዱ መኪናዎችን ጥቅም ላይ እንዲውሉ ያግዛል፡፡

የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስን ተግባር የሚጠራጠሩ ሰዎች ቴክኖሎጂው ሥራን በማደናቀፍ እና ሰዎችን በማሳሳት ሊያመጣ የሚችለውን ችግር እንደ ስጋት የሚያነሱ መኖራቸውን ሲ.ኤን.ኤን በዘገባው አስነብቧል።

ከፍተኛ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ስራ አስፈፃሚዎች ቴክኖሎጂው የሚሰራ የሰው ኃይል ያለመፈለግ አመለካከት ሊያስከትል እንደሚችል አስጠንቅቀዋል፡፡ ነገር ግን ስራ አስፈፃሚዎቹ ቴክኖሎጂውን ወደ ምርቶቻቸው ለማሰማራት እንደሚሽቀዳደሙ ዘገባው ያትታል።

በዘገባው መሠረት በዩናይትድ ስቴትስ እና በአውሮፓ ያሉ ተቆጣጣሪዎች የአርተፊሻል ኢንተለጀንስ የጥበቃ መንገዶችን ለማስቀመጥ የሚያግዝ ህግ እንዲወጣ ግፊት እያደረጉ ነው፡፡ በአውሮፓ ህብረት ውስጥ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ህግ በሚሆንበት ጊዜ, በከፍተኛ አደጋ ስርዓቶች ላይ ጥብቅ ቁጥጥር ያደርጋል።

የኢንቨስትመንት ባንክ ጎልድማን ሳችስ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ በአለም ዙሪያ ከ 300 ሚሊዮን በላይ የሙሉ ጊዜ ስራዎችን ሊተካ እንደሚችል ጠቁሟል። በሌላ በኩል አስተዳደራዊ፣ ህጋዊ፣ አርክቴክቸር እና የአስተዳደር ሚናዎች ሊጎዱ እንደሚችሉ ተናግሯል። ነገር ግን አርተፊሻል ኢንተለጀንስ የአለምን ኢኮኖሚ በ 7% ሊያሳድግ ይችላል ማለቱን ነው ቢቢሲ ያሰፈረው፡፡

ከዚህ ሌላ የህዝብ ፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት በዩናይትድ ኪንግደም ውስጥ እስከ ስምንት ሚሊዮን የሚደርሱ ሰራተኞች ቴክኖሎጂው እያደገ ሲሄድ ስራቸውን ሊያጡ እንደሚችሉ መገመቱን ቢቢሲ አስነብቧል፡፡

በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ሊተገበሩ የሚችሉ ዘርፎች በጣም ሰፊ እና የተለያዩ ናቸው። አዳዲስ የአጠቃቀም ጉዳዮች በየጊዜው እየወጡ ነው። አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ በስራ እና በግላዊነት ላይ ስላለው ተጽዕኖ በእርግጠኝነት ስጋቶች ቢኖሩም፤ የዚህ ቴክኖሎጂ ጥቅሞችን ችላ ማለት ግን ከባድ ነው።

በጥቅሉ ሰው ሰራሽ አስተውሎት አድካሚ ስራዎችን በማቅለል፣ የጤና አጠባበቅን በማሻሻል፣ በፋይናንስ ዘርፍ በቴክኖሎጂው የሚታገዙ መረጃዎችን ለመተንተን እና የፋይናንስ ተቋማት ተአማኒነት ያለው እና ትክክለኛ ውሳኔ ለመወሰን ያስችላል። እንዲሁም የተጭበረበረ ግብይትን ለመለየት እና የገበያ አዝማሚያን ለመተንበይ ይጠቅማል።

በትምህርት ዘፍርም ተጨባጭ ተጽእኖ እየፈጠረ ነው። በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ የተደገፉ የመማሪያ መድረኮች ተማሪዎች በራሳቸው ዘይቤ እና ፍጥነት እንዲማሩ እየረዳቸው ሲሆን፤ ግላዊ ግብረመልስ እና ምክሮችን ይሰጣሉ።

የሰው ሰራሽ አስተውሎት እየተሻሻለ የሚሄድ በመሆኑ ህይወታችንን ይበልጥ ቀላል እና ምቹ ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡