በሚቀጥሉት ሁለት አመታት በምግብ ራስን ለመቻል እንደ ሀገር የተጀመረው ንቅናቄ ከዳር እንዲደርስ የሁሉም አካላት ርብርብ ወሳኝ ነው – አቶ እንዳሻዉ ጣሰዉ

በሚቀጥሉት ሁለት አመታት በምግብ ራስን ለመቻል እንደ ሀገር የተጀመረው ንቅናቄ ከዳር እንዲደርስ የሁሉም አካላት ርብርብ ወሳኝ ነው – አቶ እንዳሻዉ ጣሰዉ

ሀዋሳ፡ ሰኔ 10/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በሚቀጥሉት ሁለት አመታት ተረጂነትን በማስቀረት በምግብ ራስን ለመቻል እንደ ሀገር የተጀመረው ንቅናቄ ከዳር እንዲደርስ የሁሉም አካላት ርብርብ ወሳኝ መሆኑን የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ እንዳሻዉ ጣሰዉ ተናገሩ።

የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ እንዳሻው ጣሰው “ጽዱ ከተሞች ለኢትዮጵያ ከፍታ” በሚል መሪ ቃል የከተማ ፅዳትና አረንጓዴ ልማት ንቅናቄ አስጀምረዋል።

የንቅናቄ መድረኩን በእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግር ያደረጉት የሆሳዕና ከተማ ከንቲባ አቶ ዳዊት ጡምደዶ እንደገለጹት፤ በከተማው ከጊዜ ወደ ጊዜ የህዝብ ቁጥር እየጨመረ ማምጣትን ተከትሎ የሚመነጨው ቆሻሻ ከፍ ያለ በመሆኑ እንደ ከተማ አስተዳደር ለጽዳትና ዉበት ስራዎች ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው።

በከተማ አስተዳደሩ ለአረንጓዴ ልማት የተለዩ አካባቢዎች ላልተገባ አላማ እየዋለ መሆኑን ጠቁመው በቀጣይ ችግሮቹን የማረም ስራ እንደሚሰራም ተናግረዋል።

በከተማ አስተዳደሩ በተያዘው የክረምት ወራቶች 1 ሚሊየን 220ሺህ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች በግለሰቦች መሬት በተቋማትና በሌሎች በተመረጡ አካባቢዎች እንደሚተከሉም ከንቲባው አስረድተዋል።

የሀድያ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ማቴዎስ አኒዮ እንደገለጹት፤ የሆሳዕና ከተማን ጽዱ ዉብና  ለነዋሪዎች ምቹ ለማድረግ የተጀመሩ በርካታ የመሰረተ ልማት ስራዎች አሉ።

የተጀመረው የጽዳት እና ውበት እንዲሁም ችግኝ ተከላ ስራዎች ለዜጎች የስራ እድል የሚፈጥር እና ገቢ የሚያመነጩ መሆኑንም ዋና አስተዳዳሪዉ አስረድተዋል።

የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ እንዳሻው ጣሰው በበኩላቸው ጽዱና አረንጓዴ አካባቢ መፍጠር ለኑሮ ተስማሚ አከባቢን ከማፍጠር ባለፈም የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ከፍተኛ እገዛ ያለው ነው ብለዋል።

በሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት በምግብ ራስን ለመቻል እንደ ሀገር የተጀመረው ንቅናቄ  ከዳር እንዲደርስ የሁሉም አካላት ርብርብ ወሳኝ መሆኑንም አስረድተዋል።

የሆሳዕና ከተማ በብዙ መልኩ የመልማት እድል ካላቸው ከተሞች አንዱ እንደመሆኑ በሀገር ውስጥ እና በውጭ የሚኖሩ የአካባቢው ተወላጆች ከተማዋን ተባብረው ማልማት  አለባቸው ሲሉም ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል።

ውጫዊ ብቻ ሳይሆን ውስጣዊ ጽዳትንም በመመልከት  በጋራ ለሀገር ልማት መስራት እንደሚገባም  ርዕሰ መስተዳድርሩተናግረዋል።

አንዳንድ በጽዳትና በችግኝ ተከላ ላይ የተሳተፉ የህብረተሰብ ክፍሎች በበኩላቸው ለከተማ ጽዳትና ውበት እንዲሁም ለአረንጓዴ አሻራ ልማት ስራ የራሳቸውን አስተዋጽኦ ለማድረግ ዝግጁ መሆናቸውን ተናግረዋል።

በማስጀመሪያ መርሃ-ግብሩ የክልል፣ የሀዲያ ዞን፣ የሆሳዕና ከተማ አስተዳደር ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች እንዲሁም የሆሳዕና ከተማ ነዋሪዎች ተገኝተዋል።

ዘጋቢ: ተሻለ ከበደ – ከሆሳዕና ጣቢያችን