በአቅራቢያቸው የምድብ ችሎት በመከፈቱ የተሻለ የፍትህ አገለግሎት እያገኙ መምጣታቸውን ተገልጋዮች ገለፁ

ሀዋሳ፡ ግንቦት 28/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በአቅራቢያቸው የምድብ ችሎት በመከፈቱ የተሻለ የፍትህ አገለግሎት እያገኙ መምጣታቸውን የቤንች ሸኮ ዞን የሸኮ እና የሼይ ቤንች ወረዳ ተገልጋዮች ገልጸዋል።

የፍትህ ተቋማትን ወደ ህብረተሰቡ ተደራሽ በማድረግ በኩል በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ የቤንች ሸኮ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት ገልጿል።

ካነጋገርናቸው ተገለጋዮች መካከል አቶ ጴጥሮስ ሹኒና አቶ በረከት ከበደ ከሸኮ ወርዳ የኢተቃ ምድብ ችሎት እንዲሁም አቶ አሰፋ አምቦ እና ወይዘሮ ኤሲኒ ምትኩ ከሼይ ቤንች ወረዳ የማዝ ምድብ ችሎት እንደገለፁት፤ ከዚህ ቀደም እስከ ወረዳ ድረስ ለፍትህ ፍለጋ ሂደው ለተለያዩ ወጪ ይዳረጉ እንደነበረ አውስተው አሁን ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናገረዋል።

ተገልጋዮቹ አክለውም በአቅራቢያቸው የምድብ ችሎት በመከፈቱ ከዚህ ቀደም ለትራንስፖርትና ለተለያዩ ወጪዎች ይዳረጉ ከነበርው ችግሮች ወጥተው ጊዜያቸውና ጉልበታቸውን በአግባቡ በመጠቀም የተሻለ የፍትህ አገለግሎት እያገኙ መምጣታቸውን ገልፀዋል።

በምድብ ችሎቶች አካባቢ የሚስተዋሉ የተለያዩ የግብኣት እና የባለሙያዎች እጥረትን የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ፈተው የተጀመረው አገለግሎት ተጠናክርው እንዲቀጥል ሊያደርጉ እንደሚገባም አስተያየት ሰጪዎች ጠይቀዋል።

የሸኮ ወረዳ ፍርድ ቤት ፕሬዘዳንት አቶ ምስራቅ ቢያቲ እና የሼይ ቤንች ወረዳ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት አቶ እንዳልካቸው አለማየሁ በበኩላቸው ፍርድ ቤቶች የህዝብ አመኔታን ያተረፈ እና የህግ የበላይነት የሚረጋገጥባቸው እንዲሆኑ የሚያስችል ተግባራት እየተሰራ እንደሚገኝ ተናገረዋል።

ፍትህ ፈላጊዎች ጊዜያቸውንና ጉልበታቸውን በአግባቡ ተጠቅመው ልማት ላይ እንዲውሉ በማደረግ በኩል ምድብ ችሎቶችን ወደ ህብረተሰቡ አቅራቢያ በመክፈት የፍትህ ተደራሽነት ማስፋት ሥራ እየተሰራ እንደሚገኝም የቤንች ሸኮ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት አቶ ቢኒያም ባቡ ገልፀዋል።

ዘጋቢ፡ አብዲሳ ዮናስ – ከሚዛን ጣቢያችን