በጋሞ ዞን ሕዝብ ምክር ቤት 4ኛ ዙር መርሃ-ግብር 10ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 20 መደበኛ ጉባኤ በአርባምንጭ ከተማ በመካሄድ ላይ ይገኛል

በጋሞ ዞን ሕዝብ ምክር ቤት 4ኛ ዙር መርሃ-ግብር 10ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 20 መደበኛ ጉባኤ በአርባምንጭ ከተማ በመካሄድ ላይ ይገኛል

ሀዋሳ፡ ግንቦት 01/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) ጉባኤው ለ2 ተከታታይ ቀናት የሚቆይ ሲሆን ምክር ቤቱ በአምስት ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ያፀድቃል ተብሎ ይጠበቃል።

የጉባኤውን የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የጋሞ ዞን ምክር ቤት ዋና አፈ-ጉባኤ ወ/ሪት አለሚቱ ዮሰፍ እንደተናገሩት፤ በተያዘው የበጀት ዓመት የህብረተሰቡን የልማት ጥያቄዎችን ለመመለስ በርካታ ተግባራት እንደተከናወኑ አብራርተዋል።

በተለይ ደግሞ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በግብርናው ዘርፍ የተሰራው ሥራ አበረታች መሆኑን ለምክር ቤቱ አባላትና ሌሎችም ተሳታፊዎች ገልፀዋል።

ከተመዘገቡ መልካም ተግባራት መካከል የጤናና የትምህረት መሠረተ ልማቶች በህብረተሰብ ተሳትፎ መከናወን መቻላቸውን  ጠቁመዋል።

በቀጣይም የትምህርት ስብራቱን ለመጠገን በጠቅላይ ሚኒስቴር ዐቢይ አሕመድ መሪነት የተጀመረው የመጽሐፍ ማሰባሰብ መርሃ-ግብር እንደ ዞን እየተከናወነ ያለ ቢሆንም ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ወ/ሪት አለሚቱ ለምክር ቤቱ አባላትና ለተሳታፊዎች አሳስበዋል።

በሌላ በኩል ከዴሞክራሲ ግንባታ ጋር ተያይዞ ምክር ቤቶች ያለባቸውን ትልቅ ኃላፊነት የህዝቡን የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ለመመለስ መስራት አለባቸው ነው ያሉት ዋና አፈ-ጉባኤዋ።

መሠረተ ልማቶች በአግባቡ መከናወን እንዲችሉ በተለይም ከገቢ አሰባሰብ ጋር ተያይዞ ትኩረት ሰጥቶ መስራት እንደሚገባ አጽኖት የተሰጠው ጉዳይ ነው።

በቀረበው ሪፖርት ላይ የተለያዩ ሀሳቦችን ጥያቄዎች ተሰንዝረው ከመድረኩ ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል።

የቀረበው ሪፖርት ያለተቃውሞና ያለድምፀ ታቅቦ በሙሉ ድምፅ በምክር ቤቱ አባላት ፀድቋል።

ዘጋቢ፡ ታምሩ በልሁ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን