የሚዛን ግብርና ቴክኒክ ሙያ ትምህርት ስልጠና ኮሌጅ የራሱን ገቢ አመንጭቶ ራሱን እያስተዳደረ የተሻለ ደረጃ ላይ እንዲደርስ እየተሰራ መሆኑ ተገለፀ

የሚዛን ግብርና ቴክኒክ ሙያ ትምህርት ስልጠና ኮሌጅ የራሱን ገቢ አመንጭቶ ራሱን እያስተዳደረ የተሻለ ደረጃ ላይ እንዲደርስ እየተሰራ መሆኑ ተገለፀ

ሀዋሳ፡ ግንቦት 01/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የሚዛን ግብርና ቴክኒክ ሙያ ትምህርት ስልጠና ኮሌጅ የራሱን ገቢ አመንጭቶ ራሱን እያስተዳደረ የተሻለ ደረጃ ላይ እንዲደርስ እየተሰራ መሆኑ ተገለፀ፡፡

የቴክኖሎጂ ብዜትና ሽግግር ስራም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተጠቁሟል፡፡

የኮሌጁ ዲን አቶ ካሳሁን ናይክን እንደገለፁት ኮሌጁ የራሱን ገቢ አመንጭቶ የተሻለ ደረጃ ላይ እንዲደርስ ከስራና ክህሎት ሚኒስተር በተቀመጠው አቅጣጫ መሠረት እየተሰራ ነው፡፡

ኮሌጁ ከተመሠረተ ጊዜ አንስቶ በመማር ማስተማር፣ በቴክኖሎጂ ብዜትና ሽግግር ላይ በርካታ ተግባራትን ሲያከናውን መቆየቱን አቶ ካሳሁን አስታውሰው አሁን መሬት ላይ ያሉት ሀብቶችን በማዘመን ኮሌጁ የውስጥ ገቢውን አመንጭቶ ራሱን ማስተዳደር እንዲችል ትኩረት ይሰጣል ብለዋል።

የስራና ክሎት ሚኒስቴርም ኮሌጁ ይህንን ያሳካ ዘንድ ከዚህ ቀደም በኮሌጁ ያልነበረውን የኢንተርኘራይዝ የስራ መዋቅር ፈቅዶለት ወደ ስራ ለመግባት ቅድመ ዝግጅት እየተደረገ እንደሚኝና አጫጭር ስልጠናዎችን በመስጠት ሌሎች ድጋፎችን በማድረግ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ድጋፍ እያደረገላቸው እንደሚገኝም አስረድተዋል፡፡

በዚህ መሠረትም በመደራጀት ከልማት ባንክ ገንዘብ በመበደር በቂ ማሽኖችን በማስገባት ሰፊ ስራ ይሰራል ብለዋል የኮሌጁ ዲን።

በቂጤና በኮሰኮል እንዲሁም በዋናው ግቢ ያሉት ሀብቶችን ደህንነት በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በመታገዝ መጠበቅና ተገቢውን አገልግሎት እንዲሰጡ እንደሚደረግም አቶ ካሳሁን አስገንዝበዋል፡፡

በኮሌጁ የአስተዳደርና ተማሪዎች ጉዳይ ምክትል ዲን አቶ ግርማ ለገሠ በበኩላቸው ለሰልጣኝ ተማሪዎች በተግባር ላይ የተደገፈ ስልጠና እየተሰጠ የተዘጋጁትንና በዚህ ዓመት ክረምት ወቅት መተከል የሚችሉ ከ500 ሺህ በላይ የግራቢሊያ ዛፍ ችግኞችና ከ5000 ሺህ በላይ የተመረጡ የቡና ችግኞች ለሽያጭ መዘጋጀታቸውን አስረድተዋል፡፡

ከዚህ በተጨማሪ በቋሚነት የውስጥ ገቢ ማስገኘት የሚያስችል በርካታ ሰው መያዝ የሚችል የመሰብሰቢያ አዳራሽ እየተገነባ እንደሚገኝም ገልጸዋል፡፡

ከዚህ ባለፈም የወተት ላምና የእንቁላል ዶሮ በማርባት ለአካባቢው ህዝብ ለሽያጭ ለማቅረብ ኘሮጀክት ተቀርጾ ወደ ትግበራ ለመግባት ቅድመ ዝግጅት መጠናቀቁንም አንስተዋል።

በኮሌጁ የቴክኖሎጂ ብዜትና ሽግግር ምክትል ዲን አቶ ዋለልኝ አለምነህ እንዳሉትም አካባቢው በማር ምርት የታወቀ እንደመሆኑ መጠን ከቴክኖሎጂ ብዜትና ሽግግር ስራ በተጨማሪ ገቢ ለማግኘት አሁን በኮሌጁ ውስጥ ያለውን 40 ዘመናዊ የንብ ቀፎ ወደ አንድ ሺህ ለማሳደግ ከስራና ክህሎት ሚኒስተር ጋር በመተባበር እየተሰራ ይገኛል።

በ2010 ዓ.ም በአንድ ሄክታር ማሳ ላይ ተተክሎ የነበረው የሻይ ቅጠል ተክል አሁን ምርት በመስጠት ደረጃ ላይ ስለደረሰ ያንን ፈጭቶ ለገበያ ለማቅረብና ተጨማሪ ለአካባቢው አርሶ አደር ችግኝ አዘጋጅቶ በመስጠት ምርቱን ተቀብሎ በኮሌጁ ስም በመሸጥ ገቢ ለማግኘት ሰፊ ዕቅድ ተይዞ እየተሰራ እንደሚገኝም አብራርተዋል፡፡

ዘጋቢ፡ ወሰኑ ወዳጆ – ከሚዛን ጣቢያችን