የህዝብን ሠላማዊ ግንኙነት ለማሻከር የሚሰሩ ኃይሎችን በጋራ መከላከል ይገባል- ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው
ሀዋሳ: ግንቦት 01/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የህዝብን ሠላማዊ ግንኙነት ለማሻከር የሚሰሩ ኃይሎችን በጋራ መከላከል እንደሚገባ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው ገለፁ::
ርእሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው ከቀቤና ወጣቶች ጋር በነበራቸው የውይይት መድረክ ላይ ክልሉ ቅድሚያ ሰጥቶ ከሚሰራቸው ጉዳዮች መካከል ሠላም ዋነኛው መሆኑን ጠቅሰዋል::
ቀደም ሲል በአካባቢው ተከስቶ የነበረው አይነት የፀጥታ ችግር ሊደገም የማይገባው መሆኑን ያሳሰቡት አቶ እንዳሻው የህዝብን ሠላማዊ ግንኙነት ለማሻከር የሚሰሩ ኃይሎች እንዳሉ ገልፀው እነዚህን ኃይሎች በጋራ መከላከል ያስፈልጋል ብለዋል::
ለሠላም የሚከፈለውን ማንኛውንም ዋጋ ከፍለን የህዝብን ሠላም ማስጠበቅ የኛ ድርሻ በመሆኑ ይህን እኛ እንወጣለንም ነው ያሉት:: ወጣቶችም ሠላምን በማፅናት ሂደት የድርሻቸውን እንዲያበረክቱ ጠይቀዋል::
“ከጉራጌ ወንድሞቻችሁ ጋርበሠላም ለመኖር የሚያስችሉ ሁኔታዎችን እናመቻቻለን በየደረጃው ውይይቶችም ይካሄዳሉ” ብለዋል ርእሰ መስተዳድሩ::
የውይይቱ ተሳታፊ ወጣቶች በበኩላቸው በልዩ ወረዳው ከተለያዩ መሠረተ ልማት ሥራዎች ጋርተያይዞ ጥያቄዎችን ያነሱ ሲሆን መንግስት ከሚያከናው ናቸው የልማት ሥራዎች ጎን እንደሚሰለፉ ተናግረዋል::
ወጣቱ በመደመር አስተሳሰብ ውስጣዊ አንድነቱን ማጠናከር ይኖርበታል ያሉት ደግሞ የክልሉ ረዳት የመንግስት ተጠሪ አቶ ይሁን አሰፋ ናቸው::
መደማመጥ መከባበርና መተሳሰብ ያስፈልጋል ያሉት ረዳት ተጠሪው ከሌሎች ጋር ያለውን አብሮነት አጠናክሮ ማስቀጠል እንደሚገባ ተናግረዋል::
የአዲሱ ክልል ፍሬ የሆነውን የመዋቅር ጥያቄዎችን ምላሽ ማጣጣም እንደሚያስፈልግም አስገንዝበዋል:: ይህን እድልን በመጠቀም የቀቤና ልዩ ወረዳን በሠላም በልማትና በመልካም አስተዳደር ተወዳዳሪ ማድረግ እንደሚገባ አሳስበዋል::
ይህ ትውልድ የመደመር ትውልድ በመሆኑ ከጎታች አስተሳሰቦች ተላቆ ተራማጅና ለሀገር ክብርና ልማት የሚተጋ ነው ያሉት ደግሞ የክልሉ ሠላምና ፀጥታ ቢሮ ኃላፊ አቶ ተመስገን ካሳ ናቸው::
ሃላፊው ወጣቶች በመድረኩ ገንቢ ሀሳብ ማንሳታቸውን ገልፀው በአካባቢያቸው ሠላም ላይ ግንባር ቀደም ሚና እንዲጫወቱ ጠይቀዋል::
በውይይት መድረኩ ወጣቶቹ ያነሷቸውን የልማት ጥያቄዎችን በመያዝ ተራ በተራ ምላሽ ለመስጠት እንደሚሰራበት ርእሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው ለወጣቶቹ ገልፀውላቸዋል::
ዘጋቢ ፡ ማሬ ቃጦ

More Stories
የአርሶ አደሩን የመሬት ሀብት ከፋይዳ ብሔራዊ መታወቂያ ጋር በማስተሳሰር አርሶአደሩ የፋይናንስ ተጠቃሚ እንዲሆን እየተሰራ መሆኑ ተገለጸ
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል መንግስት ጤና ቢሮ የእናቶች ጤናና የሥርዓተ-ምግብ አገልግሎት ዳይሬክቶሬት የ2018 ባጀት ዓመት ዕቅድ አፈፃፀም መድረክ በሆሳዕና ከተማ እያካሄደ ይገኛል
የከተማ አስተዳደሩ ስራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዞች ልማት ጽህፈት ቤት ወጣቶችን በማህበር በማደራጀት የኢኮኖሚ አቅማቸውን እንዲያጎለብቱ እያደረገ መሆኑን አስታወቀ