የከተማዋን ሠላምና ጸጥታ ለማስጠበቅ ሁሉም የህብረተሰብ ክፍሎች ከጸጥታ ኃይሉ ጎን በመቆም የበኩላቸውን መወጣት እንዳለባቸው ተገለጸ

የከተማዋን ሠላምና ጸጥታ ለማስጠበቅ ሁሉም የህብረተሰብ ክፍሎች ከጸጥታ ኃይሉ ጎን በመቆም የበኩላቸውን መወጣት እንዳለባቸው ተገለጸ

በጌዴኦ ዞን በይርጋጨፌ ከተማ አስተዳደር የጸጥታ ምክር ቤት ጉባዔ ተካሂዷል

በጉባኤዉ ላይ ተገኝተው የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የይርጋጨፌ ከተማ ከንቲባ አቶ ታደለ ጥላሁን ሰላም ለሁሉም ነገር አስፈላጊ በመሆኑ በመንግስት ላይ ብቻ ከመተው ይልቅ ሰላማችንን ለማስጠበቅ ሁላችንም የድርሻችንን መወጣት አለብን ነው ያሉት ።

የሰላም ተስፋ የተጣለባቸው የሃይማኖት ተቋማትም ስለ ሰላም በመስበክ፣ በማስተማር እና በመገሰጽ በሚገባ መስራት አለባቸው ያሉት ከንቲባው መንግስትም የህዝቦቹን ሰላምና አንድነትን ለማስጠበቅ እየሰራ ይገኛል ብለዋል ።

የይርጋጨፌ ከተማ አስተዳደር ሰላምና ጸጥታ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ አብዮት ተፈራ በበኩላቸዉ ከተማዋ የተረጋጋች፣ ሰላሟ የተጠበቀ እና የብዙሃን መጠለያ ለማድረግ እየተሠራ መሆኑን ጠቅሰው ሁሉም የሚመለከታቸው አካላትና ህብረተሰቡ የሚጠበቅባቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል፡፡

ከጸጥታ ምክር ቤት ጉባዔ ተሳታፊዎች መካከል አቶ አለማየሁ ደሳለኝ፣ አቶ ኃይለመስቀል ጀሞ እና ሌሎችም በሰጡት ሀሳብ ችግሮች ሲፈጠሩ የመነጋገርና የመፍታት ባህል በማዳበር ለአከባቢው ሠላም መትጋት እንደሚያስፈል ተናግረዋል፡፡

የጸጥታዉ ምክር ቤት የውይይት መድረኮችን በማዘጋጀት የህብረተሰቡን አንድነት ማጠናከርና በቤተ እምነቶች መካከል ልዩነቶች እንዳይፈጠሩ መሥራት አለባቸው ብለዋል ።

በጉባዔው ላይ የይርጋጨፌ ከተማ ሰላምና ጸጥታ ጽ/ቤት የስድስት ወራት የሥራ ዕቅድ አፈጻጸም እና ቀሪ ጊዜያት በአቶ አብዮት ተፈራ ቀርቦ ውይይት የተደረገ ሲሆን ከተሳታፊዎች ለተነሱ ጥያቄዎችም ምላሽ ተሰቶባቸዋል ።

ዘጋቢ፡ ለምለም ኦርሳ – ከይርጋጨፌ ቅርንጫፍ