ከ66 ሚሊየን በላይ የሚሆኑ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን በአረንጓዴ አሻራ ለመትከል ዝጅት መደረጉን መምሪያው አስታወቀ

ከ66 ሚሊየን በላይ የሚሆኑ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን በአረንጓዴ አሻራ ለመትከል ዝጅት መደረጉን መምሪያው አስታወቀ

ሀዋሳ፡ ሚያዚያ 10/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) ከ66 ሚሊየን በላይ የሚሆኑ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን በአረንጓዴ አሻራ ለመትከል ዝጅት መደረጉን የቤንች ሸኮ ዞን ግብርና አካባቢ ጥበቃና ህብረት ሥራ መምሪያ አስታውቋል።

ለአረንጓዴ አሻራ ሥራ ትኩረት መስጠት ለአካባቢ ደህንነትና ለምግብ ዋስትና ሚናው የጎላ እንደሆነም ተገልጿል።

በሀገራችን የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ከተጀመረበት ጊዜ ጀምሮ የሚከናወኑ ተግባራት ለአየር ንብረት የማይበገር አካባቢ እንዲፈጠር የበኩሉን ድርሻ እየተወጣ ይገኛል።

በዚህም የ2016 የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብርን የሚያሳካ 66 ነጥብ 6 ሚሊየን በላይ የሚሆኑ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች መዘጋጀታቸውን የቤንች ሸኮ ዞን ግብርና አካባቢ ጥበቃና ህብረት ሥራ መምሪያ ኃላፊ አቶ መስፍን ጉብላ ተናገረዋል።

በሆልቲካልቸር ዘርፍም ለኢኮኖሚ ጠቀሜታ ያላቸው ፍራፍሬዎች አቫካዶ፣ ማንጎ፣ ፓፓያ፣ ሙዝን ጨምሮ ከ25 ሚሊየን በላይ ችግኞች መታቀዱንም የመምሪያ ኃላፊው ገልፀዋል።

ለአረንጓዴ አሻራው መረሃ-ግብር ስኬት የማሳ ልየታ ከማደረግም ባሻገር ሰፋፊ ቦታዎችን በካረታ እየተሰራ እንደሚገኝና ፖለቲካዊ ዋጋ ያለው፣ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳና አካባቢያዊ ትርጉም ያለው ንቅናቄ ተደርጎ ወደ ተግባር እንደሚገባ አቶ መስፍን አብራርተዋል።

የአረንጓዴ አሻራ ሥራ ፋይዳው የአካባቢ ደህንነትን ለመጠበቅ፣ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ወሳኝ ሚና ያለው በመሆኑ ሁሉም በዞኑ ውስጥ ያሉት ማህበረሰቦች ዛፍ መትከል ህይወት እንደሆነ አውቆ ትኩረት ሊሰጥ እንደሚገባም ኃላፊው አስገንዘበዋል።

ዘጋቢ፡ አብዲሳ ዮናስ – ከሚዛን ጣቢያችን