ዞኑ በብድር መልክ ተሰራጭቶ ያልተመለሰ ከ144 ሚሊዮን ብር በላይ ግብረኃይል አቋቁሞ የማስመለስ ሥራ እያከናወነ ነው

ሀዋሳ፡ሚያዝያ 10/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) ከኦሞ ባንክ በመደበኛና በተዘዋዋሪ ፈንድ በብድር መልክ ተሰራጭቶ ተመላሽ ሳይደረግ የቆየ ከ144 ሚሊዮን ብር በላይ ውዝፍ ዕዳ አስመላሽ ግብረኃይል ተቋቁሞ የማስመለስ ሥራ እያከናወነ መሆኑን የጌዴኦ ዞን ሥራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዞች መምሪያ አስታወቋል፡፡

ግብረ ኃይሉ ከባድርሻ ተቋማት ጋር የአንድ ወር አፈፃፀም በይርጋጨፌ ከተማ ገምግሟል

የጌዴኦ ዞን ሥራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዞች መምሪያ ኃላፊ አቶ ተገኝ ታደሴ በተለያዩ ዘርፎች ተደራጅተው ብድር የወሰዱ ወጣቶች በተቀመጠው የጊዜ ገደብ ብድር አለመመለሳቸው አዲስ ተደራጅተው ወደ ሥራ ለሚገቡት ችግር ሆኗል ብለዋል፡፡

የተሠራጨውን የብድር ገንዘብ በመደበኛው አካሄድ መሰብሰብ ባለመቻሉ ከፌዴራል ጀምሮ በፍትህ ተቋማት የሚመራ ግብረ ኃይል ተቋቁሞ እየተሠራ መቆየቱን ጠቁመዋል፡፡

በኦሞ ባንክ የዲላ ዲስትሪክት ሥራ አስከያጅ አቶ ጌታቸው በራሶ በቁጠባ፣ በብድር ሥርጭትና አመላለስ ላይ የሚስተዋሉ ችግሮችን ለመቅረፍ በግብረ ኃይል በቅንጅት እየሠሩ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡

በዞኑ ከ2005 ዓ.ም ጀምሮ በብድር መልከ ከተሰራጨው ከ144 ሚሊዮን ብር በላይ ገንዘብ የመመለሻ ጊዜ አልፎበታል ብለዋል፡፡ ግብረ ኃይሉ ባደረገው ጥረት በአንድ ወር ውስጥ ከ5 ሚሊዮን ብር በላይ መሰብሰብ ተችሏልም ነው ያሉት፡፡

የዞኑ ፍትህ መምሪያ ኃላፊና የብድር አስመላሽ ግብረ ኃይል ሰብሳቢ አቶ ብዙአየሁ ዘውዴ በብድር ሥርጭት ወቅት ለተበዳሪዎች ተገቢ ትምህርት ካለመስጠት ጋር ተያይዞ የተፈጠረ የግንዛቤ ችግር ብድር አመላለስ ላይ አሉንታዊ ተጽዕኖ ማሳደሩን ግብረ ሀይሉ በግምገማው አመላክቷል፡፡

ብደር ላልመለሱ 127 ማህበራት ማስጠንቀቅያ መስጠታቸውንና 72 መዝገቦች የፍትሐብሔር ክስ ተመስርቶ በህግ እየታየ መሆኑም ተገልጿል፡፡

በግምገማው የተለዩ ችግሮች በፍጥነት መታረም እንዳለባቸው ግብረ ኃይሉ አሳሰቧል፡፡

ዘጋቢ፡ እምነት ሽፈራው – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን