ሀዋሳ፡ ሚያዝያ 09/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የሕብረት ሥራ ማህበራትን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ሪፎርም ለማካሄድ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል መንግስት ሕብረት ሥራ ኤጄንሲ ገለጸ።
በአንድ ሺህ መሠረታዊ ማህበራት ላይ ሪፎርም እንደሚደረግ ተጠቁሟል።
በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል 2069 መሠረታዊ ማህበራትና 21 ዩኒየኖች ይገኛሉ።
የሪፎርሙ ዓላማ የሕብረት ስራ ማህበራትን ተወዳዳሪ ለማድረግ፣ ምርትና ምርታማነትን ለመጨመር፣ የፋይናንስ አቅማቸውን ለማሳደግ፣ አሰራርን ለማሻሻልና የአባላትን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እንደሆነ የገለጹት የኤጀንሲው ዋና ዳይሬክተር አቶ ቀበሌ መንገሻ ናቸው።
በፌዴራል ሕብረት ስራ ማህበራት አደረጃጀት አዋጅ ቁጥር 788/2009 መሠረት የአንድ ሕብረት ስራ ማህበር የአባላት ቁጥር 50 መሆን ሲገባው በክልሉ ካፋ ዞን 100፤ ዳውሮ ዞን 267፤ ቤንች ሸኮ ዞን 240፤ ምዕራብ ኦሞ ዞን 33፤ ሸካ ዞን 87፤ እንዲሁም ኮንታ ዞን 61 በድምሩ 788 መሠረታዊ ማህበራት የአባላቶቻቸው ቁጥር ከደረጃ በታች መሆኑ መረጋገጡን ገልጸዋል።
አሁንም ማጣሪያ እየተደረገ ስለሚገኝ ቁጥራቸው ሊጨምር ስለሚችል እንደ ሀገር አምሳ ሺህ መሠረታዊ ማህበራት ላይ ሪፎርም ለማድረግ ከታቀደው ውስጥ እንደ ደቡብ ምዕራብ ክልል አንድ ሺህ መሠረታዊ ማህበራት ላይ ሪፎርም እንደሚደረግ አስገንዝበዋል።
ሪፎርሙ በ2016 በጀት ዓመት ቀሪ ወራት የሚካሄድ ሆኖ በፌዴራል ደረጃ የተሰጠውን የግንዛቤ ማስጨበጫ ወደ ዞኖች በማውረድ በክልሉ የሚገኙ ስድሰት ዞኖችን በሁለት ጎራ በመመደብ ለግብርና አካባቢ ጥበቃና ሕብረት ስራ መምሪያ ኃላፊዎችና ምክትሎቻቸው ስልጠና መስጠቱን ዋና ዳይሬክተሩ ገልጸዋል።
ማህበራቱ ካፒታላቸው 800 ሚሊዮን ብር መድረሱን አቶ ቀበሌ ጠቁመው ሪፎርሙ ከተካሄደ በአንዳንድ ዩኒየን አባላት መካከል ከሀብት ክፍፍል ጋር ተያይዞ የተፈጠረውን አለመግባባት ይፈታል ተብሎ እንደሚታመን አቶ ቀበሌ አክለው አብራርተዋል።
ዘጋቢ፡ ወሰኑ ወዳጆ – ከሚዛን ጣቢያችን

More Stories
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አንዳንድ አካባቢዎች በተደረገ ድንገተኛ ፍተሻ 25 ሺህ 338 ሊትር ቤንዝልና 62 ሺ 686 ሊትር ናፍጣ በቁጥጥር ስር መዋሉን የክልሉ ንግድና ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ አስታወቀ
ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ሰላማዊ፣ ፍትሐዊና ዴሞክራሲያዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ የፍትህና የጸጥታ ዘርፍ አመራሮችና ባለሙያዎች ሚና የላቀ መሆኑ ተገለጸ
ከአየር ንብረት ተፅዕኖ ጋር እየተስተዋሉ ያሉትን ችግሮች ለመከላከል ሁሉም የበኩሉን ሊወጣ እንደሚገባ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አካባቢ ጥበቃና የአየር ንብረት ለውጥ ባለስልጣን አስታወቀ