በቴክኒክና ሙያ ስልጠና ተቋማት ውስጥ ያሉ የስልጠና ማሽነሪዎች በሚገባቸው ልክ ለታለመላቸው አላማ እየዋሉ አለመሆናቸው ተገለፀ

የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና ቢሮ በክልሉ ይህን ክፍተት ለመድፈን ያለመ ስልጠና በሾኔ ከተማ መስጠት ጀምሯል።

የቢሮው ምክትል ሀላፊና የተቋማት አቅም ግንባታና ስልጠና ዘርፍ ሀላፊ አቶ ሰለሞን ፈርሻ እንደገለፁት ሀገሪቷ በከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ የገዛቻቸው ማሽኖች ተገቢውን አገልግሎት እየሰጡ አይደለም።

በዚህም እንደሀገር ከፍተኛ ኪሳራ እያስተናገድን ነው ያሉት ምክትል ሀላፊው በክልሉ ባሉ 38 የቴክኒክና ሙያ ማስልጠኛ ኮሌጆች ውስጥ ያሉ ማሽነሪዎችን በአግባቡ በመጠቀም ለታለመለት አላማ ማዋል ይገባል ብለዋል።

የተገዙ ማሽኖች ከመጡ በኋላ አገልግሎት ላይ ሳይውሉ ለበርካታ አመታት መጋዘን ውስጥ መቀመጣቸው ሌላኛው ችግር መሆኑን ተናግረው ይህም መቀረፍ አለበት ብለዋል።

እየተሰጠ ያለው ስልጠናም በየኮሌጁ ያሉ ማሽነሪዎች ወደ ስራ ገብተው ተገቢውን አገልግሎት እንዲሰጡ ምቹ ሁኔታ ይፈጥራል ብለዋል።

ስልጠናው ከሀዋሳ ዩኒቨርስቲ እና ከኢትዮ-ኢንጂነሪንግ ግሩፕ በመጡ አሰልጣኞች እየተሰጠ ነው።

ዘጋቢ: ጀማል የሱፍ