የስርጭት መጠኑ እየጨመረ የመጣውን የኤች አይ ቪ ቫይረስ ስርጭት ለመግታት ይበልጥ ትኩረት እንደሚሻ ተገለጸ

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልላዊ መንግሥት ጤና ቢሮ ከኢፌዲሪ ጤና ሚኒስቴር ጋር በመተባበር የማህበረሰብ መሪነት ለላቀ የኤች አይ ቪ መከላከል በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀ ክልላዊ የንቅናቄ መድረክ በአርባ ምንጭ ከተማ ተካሂዷል።

ለኤች አይ ቪ በሽታ ይበልጥ ተጋላጭ የሆኑ የህበረተሰብ ክፍሎች የደም ምርመራ አድረገው ራሳቸውን እንዲያውቁ በማድረግ የቫይረሱን ስርጭት ለመከላከል ሁሉም የበኩሉን እንዲወጣ ጥሪ ቀርቧል።

በኤች አይ ቪ ዙሪያ እየተስተዋለ ያለው መዘናጋት ካልተቀረፈ በአሳሳቢነት ደረጃ ላይ መድረሱን የክልሉ ጤና ቢሮ ሀላፊ አቶ እንደሻው ሽብሩ ተናግረዋል።

ስርጭቱን ለመግታት ይበልጥ ተጋላጭ የሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎች ላይ የሚደረገው የግንዛቤ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የቢሮ ሀላፊው ገልጸዋል።

በንቅናቄው መድረክ ላይ ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መንግሥት ዋና ተጠሪ አቶ ዓለማየሁ ባውዲ በበኩላቸው ቫይረሱ ምርታማ የሆነውን ወጣት በማጥቃት ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ጉዳት እያደረሰ በመሆኑ የመከላከሉን ሥራ በትኩረት ለመሥራት መታቀዱን ገልጸዋል።

ፈቃደኝነት ላይ የተመሠረተ የደም ምርመራ በማድረግ ቫይረሱ በደማቸው ያለባቸውን ሰዎች የፀረ-ኤች አይ ቪ ኤድስ መድሀኒት እንዲጀምሩ ማድረግና የግንዛቤውን ሥራ ይበልጥ ለማጠናከር ክልላዊ ማቀጣጠያ ፕሮግራም እስከ ቀበሌ ድረስ በአግባቡ መምራት እንደሚገባም ተብራርቷል።

በክልሉ በ2030 ኤች አይ ቪ የጤና ስጋት ወደማይሆንበት ደረጃ ላይ ለማድረስ ታቅዶ እየተሠራ ስለመሆኑም ተብራርቷል።

ዘጋቢ፡ ወ/ገብርኤል ላቀው – ከአርባ ምንጭ ጣቢያችን