ሞዴል የሆኑ የአገልግሎት ተቋማትን በመገንባት የዘመነ አገልግሎት ለህብረተሰቡ ለመስጠት እየተሰራ እንደሚገኝ የክልሉ ከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ አስታወቀ

ሞዴል የሆኑ የአገልግሎት ተቋማትን በመገንባት የዘመነ አገልግሎት ለህብረተሰቡ ለመስጠት እየተሰራ እንደሚገኝ የክልሉ ከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ አስታወቀ

ሀዋሳ፡ መጋቢት 27/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) ሞዴል የሆኑ የአገልግሎት ተቋማትን በመገንባት የዘመነ አገልግሎት ለህብረተሰቡ ለመስጠት እየተሰራ እንደሚገኝ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ አስታወቀ።

ቢሮው በክልሉ በሚገኙ 5 ከተሞች ሲያደርግ የነበረውን የመስክ ምልከታ አጠናቋል። በአርባምንጭ ከተማ የመሠረተ ልማት ግንባታ ሥራዎች ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ብርሃኑ ዘውዴ እንዳሉት፤ ሞዴል የሆኑ የአገልግሎት ተቋማትን በክልሉ ከተምች በማስፋት የዘመነ አገልግሎት ለህብረተሰቡ ለመስጠት እየተሰራ ይገኛል።

ያልተጠናቀቁ ፕሮጀክቶችም ፈጥነው ወደ ተግባር መግባት እንዳለባቸው አሳስበዋል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ ም/ኃላፊና የማስፈፀም ዘርፍ ኃላፊ ወ/ሮ የምስራች ገመዴ በበኩላቸው በክልሉ የመሰረተ ልማት ጉድለቶችን በመለየት ህብረተሰቡን የመሰረተ ልማት ጥያቄን የሚፈቱ ስራዎች መሰራታቸውን ገልጸዋል።

በቀጣይም ያልተጠናቀቁ ፕሮጀክቶችን በማጠናቀቅ ህብረተሰብ ተኮር ስራዎች እንደሚሰሩ አረጋግጠዋል።

የአርባምንጭ ከተማ አስተዳደር በ2016 በበጀት ዓመት ከ201 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ በማድረግ የመሠረተ ልማት ሥራዎችን እያከናወነ ይገኛል ያሉት የከተማዋ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ገዘኸኝ ጋሞ ናቸው።

እንደ ከንቲባው ገለፃ እየተገነቡ ያሉ መሠረተ ልማቶች ለከተማው ውበት ከመስጠት ባሻገር ለብዙ ሰዎች ሥራ ዕድል እንደፈጠረላቸውና ሥራዎች በአጭር ጊዜ ውስጥ ተጠናቀው ለህብረተሰቡ አገልግሎት መስጠት እንዲችሉ ክትትል ይደረጋል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ም/ቤት የፕላን መሠረተ ልማት እና የመንግስት ሀብት አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ስብሳቢ አቶ ዕንቁ ዮሐንስ በክልሉ 5 ከተሞች ከተሞችን ፅዱ ሳቢና ለነዋሪዎች ምቹ ለማድረግ በርካታ አበረታች ተግባራት መከናወናቸውን አውስተው በቀጣይም ተጠናቀው የመልካም አስተዳደር ችግሮችን በሚፈቱ መልኩ ሊከናወኑ ይገባል ብለዋል።

በአርባምንጭ ከተማ በተፈጠረላቸው የስራ ዕድል ተጠቅመው በመስራት ላይ የሚገኙት ወጣት ያዕቆብ ጌታሁንና ባህታ መንገሻ ገለፃ በከተማው በተፈጠረው ስራ ተጠቃሚ መሆን ችለዋል።

በቀረቡት ጥያቄዎችና አስተያየቶች ላይ ቢሮው ተገቢውን ማብራሪያና ምላሽ የሰጠ ሲሆን በጉድለት የተነሱትን ጉዳዮች በቀጣይ በልዩ ትኩረት የዕቅድ አካል ተደርጎ ይሰራል ተብሏል፡፡

ዘጋቢ፡ ተመኙህ ገረሱ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን