ግብርን በወቅቱ እና በታማኝነት በመክፈል ለከተማው እድገት ሀላፊነታችንን እየተወጣን ነው – የሰላምበር ከተማ ግብር ከፋዮች

ግብርን በወቅቱ እና በታማኝነት በመክፈል ለከተማው እድገት ሀላፊነታችንን እየተወጣን ነው – የሰላምበር ከተማ ግብር ከፋዮች

ሀዋሳ፡ መጋቢት 13/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) ግብርን በወቅቱ እና በታማኝነት በመክፈል ለከተማው እድገት ሀላፊነታቸውን እየተወጡ መሆኑን የሰላምበር ከተማ ግብር ከፋዮች ተናገሩ።

የገቢ ጉዳይ በከተማ አስተዳደሩ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት የሚመራ መሆኑን ከተማ አስተዳደሩ አስታውቋል።

ግብር ለአንድ ሀገር እድገት እና ልማት የጀርባ አጥንት መሆኑ ይታመናል።

በሰላምበር ከተማ ተዘዋውረን ካነጋገርናቸው ግብር ከፋዮች መካከል አቶ ተስፋዬ ጫልኤቦ እንደገለፁት ግብርን በወቅቱና በታማኝነት በመክፈል ሀገራዊ ሀላፊነታቸውን አየተወጡ መሆኑን በመግለጽ በዚህም ግንባር ቀደም በመሆኔ ተሸላሚ ሆኛለው ብለዋል።

ሌላይኛው ግብር ከፋይ አቶ መለሰ መጃ ከምናገኘው ገቢ ላይ የሚጠበቅብንን በመክፈል መንግስት የሚያከናውናቸው የልማት ስራዎች እንዲፋጠኑ ማድረግ ይጠበቅብናል ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።

የደረሰኝ ማሽን ግዢ ለመፈፀም ፍላጎት ብናቀርብም በአቅራቢው ድርጅት በኩል ምላሽ በመቆየቱ የእጅ በእጅ ደረሰኝ አየተጠቀምን ቢሆንም የሚመለከተው አካል ምላሽ ቢሰጠን ሲሉ አቶ መለሰ ጠይቀዋል።

የሰላምበር ከተማ ገቢዎች ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ተረፈ ሳዴቦ በከተማው በአመቱ ውስጥ 75ሚሊየን 566ሺህ 142 ብር ለመሰብሰብ ከታቀደው መደበኛ ገቢ 47ሚሊየን 948ሺህ 201ብር መሰብሰብ መቻሉን በመግለጽ አፈፃፀሙም 63% መሆኑን አስረድተዋል።

ከማዘጋጃቤታዊ ገቢ40ሚሊየን 583ሺህ 154ብር በአመቱ ውስጥ ለመሰብሰብ ከታቀደው 11ሚሊየን 485 ሺህ17 ብር በመሰብሰቡ አፈፃፀሙ 28%ላይ የሚገኝ ሲሆን በቀሪ ጊዜያት በሙሉ አቅም በመስራት አፈፃፀሙን ከፍ ማድረግ እንደሚገባ ገልፀዋል።

ከደረሰኝ ጋር ተያይዞ ወንዶ ኩባንያ ብቻ የሚያቀርብ ሲሆን ጽ/ቤቱ ለሚመለከተው አካል ማሳወቁንም አቶ ተረፈ አስረድተዋል።

የሰላምበር ከተማ ከንቲባ አቶ ዘነበ ወንቴ በበኩላቸው የገቢ አሰባሰብን የከተማ አስተዳደሩ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ የሚሰራው ተግባር መሆኑን ገልፀዋል።

ግንባር ቀደም ግብር ከፋዮችን እውቅና በመስጠት ሌሎችም እንዲነሳሱ የማድረጉ ተግባር የሚቀጥል በመሆኑ ሁሉም አካል የሚጠበቅበትን ግብር በወቅቱና በሀላፊነት ስሜት እንዲከፍል ጥሪ አቅርበዋል።

ዘጋቢ፡ ገነት መኮንን – ከአርባምንጭ ጣቢያችን