“ኢትዮጵያ በሁሉም አካባቢዎች ውብ ናት” – ዶ/ር አለሙ ስሜ

“ኢትዮጵያ በሁሉም አካባቢዎች ውብ ናት” – ዶ/ር አለሙ ስሜ

ሀዋሳ፡ መጋቢት 12/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) ሀምበርቾ 777 የጎበኙት የትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ሚኒስትር ዶ/ር አለሙ ስሜ ዘርፈ ብዙ ትርጉምና ፋይዳ ያለው መሆኑን ገልጸዋል።

777ቱንም የተራራው መውጫ ደረጃዎችን ተራሞደው ተራራው አናት ላይ የወጡት ሚኒስትሩ “ኢትዮጵያ በሁሉም አካባቢዎች ውብ ናት” ሲሉ ተናግረዋል። “ደረጃውን ወጥቼ በመጨረሴም ደስ ብሎኛል” ነው ያሉት ሚኒስትሩ።

በሀገራችን በርካታ ተራራዎችና የሚያምሩ መልክዓ ምድሮችን አልምተን የቱሪዝም የገቢ ምንጭ ማድረግ እየተቻለ ነገር ግን ለበርካታ አመታት ሳንጠቀምበት ቀርተናል ሲሉ ገልጸዋል።

ከለውጡ ወዲህ በተለይም ጠቅላ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ ከግቢያቸው  ጀምሮ በተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች የኢትዮጵያን እምቅ የተፈጥሮ አቅም ማሳየት የቻለ፣ ገፅታዋን የቀየረና ቱሪስትን መሳብ የሚችል ሥራ ማከናወን ችለዋል ነው ያሉት ዶ/ር አለሙ ስሜ።

ሌሎችም በየደረጃው ያለን አመራሮች ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከአዲስ አበባ ጀምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ያለሟቸውን የቱሪዝም ፕሮጀክቶች በምሳሌነት በመውሰድ ለሀገር እድገት የሚጠበቅብንን ማበርከት ይኖርብናል ሲሉ አስገንዝበዋል።

የሀምበርቾ 777 ኢኮ ቱሪዝም የዚህ ማሳያ ነው ያሉት ዶ/ር ዓለሙ  ታሪክ ያለው  ለመዝናኛም ለጤናችንም የሚሆን ድንቅ ቦታ ነው ብለዋል።

አክለውም አሁንም  ማረፊያ ሎጆች፣ ማደሪያ መኝታዎች እና በአካል ጉዳትም ሆነ በተለያዩ ችግሮች ተራራውን መውጣት ላልቻሉ ወገኖችም ምቹ ማድረግን እንደሚጠይቅ ተናግረዋል።

ከተሠራበት ከዚህ በላይ ውብና በርካታ ቱሪስት እንዲስብ ማድረግ ይቻላልም ብለዋል።

ዘጋቢ፡ ማሬ ቃጦ