ወንጀልን በጋራ በመከላከል ረገድ ሕብረተሰቡ ከፖሊስ ጎን በመቆም ተቀናጅቶ መስራት እንዳለበት ተገለፀ

ወንጀልን በጋራ በመከላከል ረገድ ሕብረተሰቡ ከፖሊስ ጎን በመቆም ተቀናጅቶ መስራት እንዳለበት ተገለፀ

ሀዋሳ፡ መጋቢት 12/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) ወንጀልን በጋራ በመከላከል ረገድ ሕብረተሰቡ ከፖሊስ ጎን በመቆም ተቀናጅቶ መስራት እንዳለበት ተገልጿል።

የይርጋጨፌ ወረዳ ፖሊስ ጽህፈት ቤት ወንጀልን ለመከላከል የሰላም ምክር ቤት አቋቁሞ ወደ ሥራ መግባቱን አስታውቋል።

የይርጋጨፌ ወረዳ ፖሊስ  አዛዥ ዋና  ኢንስፔክተር  ታምራት ምትኩ እንደተናገሩት፤ ወንጀልን ለመከላከል  ከሕብረተሰቡ ጋር  በተደረጉ ውይይቶችና የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎች መነሻ በርካታ ወንጀልን  ከመከላከል አኳያ የተገኙ ውጤቶች መኖራቸውንና በቀጣይም ተጠናክሮ ይቀጥላል።

አክለውም በተደረገው ወንጀልን የመከላከል ሥራ እንደ ወረዳ  በሌብነት ወንጀል 72 አቤቱታዎች ቀርበው የክስና የምርመራ ሂደት ተጠናቆ 75 ወንጀለኞች ላይ በይርጋጨፌ ወረዳ የመጀመሪያ  ደረጃ ፍርድ ቤት ከ8 ወር እስከ 5 ዓመት  ውሳኔ በማግኘት  በማረምያ ቤት የሚገኙ መሆኑን አስረድተዋል።

በተለይም አርሶ አደሩ የቡናን ምርት በሚሰበስብበት ወቅት የሚፈፀሙ ወንጀሎች በርካታ ከመሆናቸው መነሻ  በበልግ የእርሻ ምርትና ዝግጅት ወቅት ለልማቱ ስኬት ተግዳሮት የሚሆኑ የሌብነት ወንጀሎችን  ለመከላከል ሕዝቡ ከፖሊስ ጋር በቅንጅት መሥራት እንዲችል የሰላም ምክር ቤት በማቋቋም ከወረዳ አስከ ቀበሌና ህዋስ ድረስ የፖሊስ አባላትን ምደባ በማድረግ  በትኩረት እየሠራ መሆኑን አዛዡ አስረድተዋል።

የይርጋጨፌ ወረዳ ፖሊስ ጽህፈት ቤት ኢንዶክትርኔሽንና የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ዋና ሳጅን ኢዮብ አየለ በበኩላቸው፤ ወንጀልን  ለመከላከል ከሕብረተሰቡ ጋር በመቀናጀት በሜይንስትሪሚንግ ኮሚቴ በየደረጃው የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዋችን በመሥራት   ሕዝቡ ለሰላሙና ለልማቱ ተግዳሮት የሚሆኑ ወንጀሎችን ከመከላከል ረገድ  ለውጥ መታየት ችሏል ነው ያሉት።

በቀጣይም ከሚመለከታቸው አካላት ጋር የመከላከል ተግባሩ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አብራርተዋል።

ዘጋቢ፡ ፅጌ ደምሴ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን