ብልጽግና ፓርቲ በምርጫ ወቅት ለህዝቡ የገባውን ቃል ወደ ተግባር በመለወጥ ስኬት እያስመዘገበ እንደሚገኝ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል አመራር አካዳሚ ዋና ዳይሬክተር አቶ ተስፋዬ ብላቱ ገለፁ

ብልጽግና ፓርቲ በምርጫ ወቅት ለህዝቡ የገባውን ቃል ወደ ተግባር በመለወጥ ስኬት እያስመዘገበ እንደሚገኝ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል አመራር አካዳሚ ዋና ዳይሬክተር አቶ ተስፋዬ ብላቱ ገለፁ

”ቃልን በተግባር ለኢትዮጵያ ብልጽግና” በሚል መሪ ቃል በክልሉ የሳጃ ክላስተር የክልል ቢሮዎች መሠረታዊ ድርጅት አባላት ኮንፈረንስ ተካሂዷል።

በኮንፈረንሱ ላይ የተገኙት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል አመራር አካዳሚ ዋና ዳይሬክተር እና የሳጃ ክላስተር መሠረታዊ ድርጅት ሰብሳቢ አቶ ተስፋዬ ብላቱ የብልጽግና ፓርቲ ባለፉት ሁለት አመት ከግማሽ ጊዜያት በገጠርም ሆነ በከተማ ለህዝቡ የገባውን ቃል በተግባር በማረጋገጥ ስኬት እያስመዘገበ ይገኛል ብለዋል።

የኮንፈረንሱ አላማ በፓርቲው የተመዘገቡ ዉጤቶችን በማጠናከርና ያልተከናወኑ ተግባራትን በመለየት በፖለቲካ፣ በማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ መስኮች ላይ የአባላቱ ሚና ምን መሆን እንዳለበት በመነጋገርና በመመካከር በቀጣይ የተሻለ ስራ ለመስራት ያለመ እንደሆነም አቶ ተስፋዬ ገልጸዋል።

የክልሉ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ምክትልና የቱሪዝም ዘርፍ ሀላፊ እንዲሁም የሳጃ ክላስተር መሠረታዊ ድርጅት ምክትል ሰብሳቢ እና የፖለቲካ ዘርፍ ሀላፊ አቶ ኑሪ ከድር በበኩላቸው ከአንዱ ስኬት ወደ ቀጣዩ ስኬት ለመሸጋገር የፓርቲው አመራሮችና አባላት የማይተካ ሚና እንዳለቸው ተናግረዋል።

ከዉይይቱ የተገኙ ተጨማሪ ግብአቶችን በአግባቡ በመጠቀም በመሠረተ ልማትና በሰላም እሴት ግንባታ እንዲሁም የዉይይት ሂደትን ለማጎልበት የሚያስችሉ ስራዎችን መስራት የቀጣይ የትኩረት ዘርፎች መሆናቸውን አቶ ኑሪ ጠቁመዋል።

በኮንፈረንሱ የፓርቲው የግማሽ የምርጫ ዘመን አፈጻጸም እና የቀሪ ምርጫ ዘመን ዋና ዋና የትኩረት መስኮች ረፖርት ቀርቦ ሰፊ ዉይይት ተደርጎበታል።

ከኮንፈረንሱ ተሳታፊዎች መካከል አቶ አበራ መኩሪያ፣ ወ/ሮ ጌጤነሽ አስፋው እና አቶ ሩፋኤል ንዥናጋ በሰጡት አስተያየት ፓርቲዉ እስካሁን በሁሉም የልማት ዘርፎች ያከናወናቸው ተግባራት እና ያጋጠሙ ተግዳሮቶች ዙሪያ በቂ ግንዛቤ ማግኘታቸውን ጠቁመው ለተጀመረው ሁለንተናዊ የብልጽግና ጥረት ስኬታማነት የተጠናከረ ርብርብ ለማድረግ መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል።

ዘጋቢ፡ ብርሃኑ ማሞ – ከወልቂጤ ጣቢያችን