የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት የህገ-መንግስት ጉዳዮች አጣሪ ጉባኤ ሰየመ

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት የህገ-መንግስት ጉዳዮች አጣሪ ጉባኤ ሰየመ

ሀዋሳ፡ መጋቢት 05/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት በ6ኛ ዙር 3ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 2ኛ መደበኛ ጉባኤ የህገ-መንግስት ጉዳዮች አጣሪ ጉባኤ እንዲሆኑ በክልሉ ርዕሰ መስተዳድር የቀረበለትን 6 እጩዎች ኮሚቴው ተቀብሎ አጽድቋል።

በዚህ መሠረት፦ አማረ አንጆ፣ ክብሩ ማሞ፣ ስጦታው ጋርሾ፣ ኩታዬ ኩሲያ፣ በለም ገብሬና ካሳሁን ፍልፍሉ የህገ-መንግስት ጉዳዮች አጣሪ ኮሚቴ ሆነው እንዲያገለግሉ ርዕሰ መስተዳድሩ አቅርበዋል።

የምክር ቤቱ አባላትም የቀረቡ እጬዎች ያላቸው የስራ ልምድና የትምህርት ዝግጅት ለዚሁ ተግባር የሚመጥን በመሆኑ ምክር ቤቱ በሙሉ ድምጽ ተቀብሎ አጽድቋል።

ከዚህ በተጨማሪ በምክር ቤቱ በተጓደለ የፌደሬሽን ም/ቤት አባል ምትክ፥ ከክልሉ ምክር ቤት ይመረጣል በሚለው መሠረት አቶ ሳሙኤል ፎላን የፌደሬሽን ምክር ቤት አባል እንዲሆኑ በሙሉ ድምጽ ተቀብሎ አጽድቋል።

በሌላ በኩል የአንድ የምክር ቤት አባል ያለመከሰስ መብት ከለላ እንዲነሳ የክልሉ ፍትህ ቢሮ በጠየቀው መሠረት፥ አቶ እስራኤል በይሳ ከባስኬቶ እና አማኒያስ ጎሹና ከጋሞ ዞን በሠሩት ወንጀል እጅ ከፍንጅ መያዛቸውን ተከትሎ ያለመከሰስ ከለላቸው እንዲነሳ የክልሉ ፍትህ ቢሮ ጠይቋል።

ምክር ቤቱም የቀረበለትን ያለመከሰስ መብት ከለላ ተቀብሎ በ2 ተቃውሞ እና በ6 ድምጸ ተዓቅቦ በማጽደቅ፥ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት በ6ኛ ዙር 3ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 2ኛ መደበኛ ጉባኤውን አጠቃሏል።

ዘጋቢ፡ ዘላለም ተስፋዬ