የግብርናና ገጠር ልማት ቋሚ ኮሚቴ ለደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት ያቀረባቸውን 5 አዋጆች ምክር ቤቱ አጸደቀ

የግብርናና ገጠር ልማት ቋሚ ኮሚቴ ለደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት ያቀረባቸውን 5 አዋጆች ምክር ቤቱ አጸደቀ

ሀዋሳ፡ መጋቢት 05/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት 6ኛ ዙር 3ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 2ኛ መደበኛ ጉባኤ የግብርናና ገጠር ልማት ቋሚ ኮሚቴ ያቀረባቸውን 5 አዋጆች ተቀብሎ አጽድቋል።

ረቂቅ አዋጆቹን በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት የግብርናና ገጠር ልማት ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ጠንክር ጠንካ የ5ቱን አዋጆችና ዝርዝር ይዘት ለምክር ቤቱ አቅርበዋል።

የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ አቶ ጠንክር ጠንካ፥ ለምክር ቤቱ በሰጡት ማብራሪያ፥ የረቂቅ አዋጆቹን አስፈላጊነት በዝርዝር አስረድተዋል።

ረቂቅ አዋጆቹ በቋሚ ኮሚቴዎች አማካኝነት ተገቢው ውይይት እና ምክክር የተደረገባቸው ሲሆን፥ የክልሉን ነባራዊ ሁኔታ ከግምት ውስጥ በማስገባትና የህዝቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ እንዲሁም ከክልሉ ህገ መንግስት ጋር እንዲጣጣሙ ተደርገው መዘጋጀታቸውን አቶ ጠንክር ለም/ቤቱ ገልፀዋል።

በዚህም መሰረት ምክር ቤቱ የቀረበለትን 5 ልዩ ልዩ የግብርናና ገጠር ልማት ቋሚ ኮሚቴ ረቂቅ አዋጆችን መርምሮ አጽድቋል።

1, የደቡብ ኢትጵያ ክልላዊ መንግስት የኮንሶ ባህላዊ መልክአ-ምድር ቅርሶችን ለመጠበቅ የወጣ ረቂቅ አዋጅ፣

2, የደቡብ ኢትጵያ ክልላዊ መንግስት የጌዴኦ ባህላዊ መልክአ-ምድር ቅርሶችን ለመጠበቅ የወጣ ረቂቅ አዋጅ፣

3, የደቡብ ኢትጵያ ክልላዊ መንግስት የማዕድን ስራዎችን ለማስተዳደር የወጣ አዋጅ፣

4, የደቡብ ኢትጵያ ክልላዊ መንግስት የዱር ህይወት ጥበቃ፣ ልማትና አጠቃቀም አዋጅ፣

5, የደቡብ ኢትጵያ ክልላዊ መንግስት የውሃና ፍሳሽ አገለግሎት ድርጅት አዋጅ

በቀሩቡት አዋጆች ዙሪያ የምክር ቤት አባላት በተነሱ ጥያቄዎች ላይ ተጨማሪ ሃሳብና አስተያየት የሰጡበት ሲሆን፥ አዋጆቹ ተጨማሪ ግብዓት ታክሎባቸው ም/ቤቱ በሙሉ ድምጽ ተቀብሎ አጽድቋል።

ዘጋቢ፡ ዘላለም ተስፋዬ