በሴቶች ላይ የሚደርስ ጥቃትና ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶችን ማስቀረት የሁሉንም ርብርብ የሚጠይቅ ነው- የደቡብ ኦሞ ዞን አስተዳደር

በሴቶች ላይ የሚደርስ ጥቃትና ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶችን ማስቀረት የሁሉንም ርብርብ የሚጠይቅ ነው- የደቡብ ኦሞ ዞን አስተዳደር

ሀዋሳ፡ መጋቢት 04/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) “ሴቶችን እናብቃ ልማትና ሰላምን እናረጋግጥ” በሚል መሪ ቃል ከወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ  ጋር በመተባበር የሴቶች ቀን በዲመካ ከተማ እየተከበረ ይገኛል።

በአሉን አስመልክቶ በተዘጋጀው መድረክ ላይ የደቡብ ኦሞ ዞን ሴቶችና ህጻናት ጉዳይ መምሪያ ኃላፊ ወ/ሮ መስታዋት በዛብህ እንዳሉት በዞኑ በርካታ ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች መኖራቸውን ጠቅሰው ድርጊቱን ለማስቀረት ሰፊ ስራ ሊሰራ ይገባል ።

በተለይም የሴቷ ተሳትፎና ተጠቃሚነት ላይ ትልቅ ስራ ሊሰራ እንደሚገባ የሚናገሩት ወ/ሮ መስታዋት ዛሬም ሴቷ ሀብት የማፍራት እና በባለቤትነት መምራቷ እነደ ነውር የሚቆጠር በመሆኑ በዚህ ረገድ ሰፊ ስራ ይጠይቃል ብለዋል።

በመሆኑም የሴቶች ቀንን ስናከብር በሴቶች ላይ የሚደርሰውን ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች በማስቀረትና የሴቷን ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ሊሆን እንደሚገባም አስገንዝብዋል ።

የዞኑ ዋና አስተዳደሪ አቶ ማዕከል ማሊኮ በበኩላቸው በዞናችን ጎጂ ልማዳዊ ድርጊት አሁን ላይ እየቀነሰ ቢሆንም ሙሉ በሙሉ  ለማስቀረት ርብርብ ልናደርግ ይገባል ብለዋል።

ሴቶች ላይ የምንሰራው ስራ ለሁሉም ስራ ስኬት በመሆኑ እንደ ዞን ጥረቱ ሊቀጥል እንደሚገባ አጽንኦት ሰጥተዋል።

የወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ የደቡብ ኦሞ  ክላስተር ማስተባበርያ ቢሮ ፕሮግራም ማናጀር  አቶ አለማየሁ ብርሀኑ የማህበረሰቡን ንቃተ ህሊና በማስፋት ሚንጊ ተብለው ለሚጣሉና ለሚሞቱ ህጻናት ድምጽ ልንሆናቸው ይገባል ብለዋል።

በበአሉ ላይ ከሁሉም ወረዳዎች የተዉጣጡ የማህበረሰብ ክፍሎች አመራሮችና ባለ ድርሻ አካላት ተሳታፊ ነበሩ።

ዘጋቢ ፡ ማርታ ሙሉጌታ- ከአርባምንጭ ጣቢያችን