የዜጎችን የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥና የሥራ አጥነት ችግርን ለመቅረፍ ሁሉም ባለድርሻ አካላት ተቀናጅተው መሥራት ወሳኝ መሆኑ ተገለጸ

የዜጎችን የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥና የሥራ አጥነት ችግርን ለመቅረፍ ሁሉም ባለድርሻ አካላት ተቀናጅተው መሥራት ወሳኝ መሆኑ ተገለጸ

ሀዋሳ፡ መጋቢት 03/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የዜጎችን የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥና የሥራ አጥነት ችግርን ለመቅረፍ ሁሉም ባለድርሻ አካላት ተቀናጅተው መሥራት ወሳኝ መሆኑ ተገልጿል።

የጌዴኦ ዞን የሥራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕሪይዞች ልማት መምሪያ ከኦሞ ባንክ ዲላ ዲስትሪክት ጋር  በመተባበር የሥራ ዕድል ፈጠራ ንቅናቄ መድረክ  አካሂዷል።

የንቅናቄ መድረኩን በንግግር የከፈቱት የጌድኦ ዞን የኦሞ ባንክ የዲላ ዲስትሪክት ሥራ አስኪያጅ  አቶ ጌታቸው በራሶ፤ የዜጎችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ ባለድርሻ አካላት ከምንጊዜውም በላይ በቅንጅትና በትኩረት መሥራት እንደሚጠበቅባቸው ተናግረዋል።

በመድረኩ የ8 ወር አፈጻጸም ሪፖርት ቀርቦ የተገመገመ ሲሆን በቁጠባ እና በብድር አመላለስ ዝቅተኛ አፈፃጸም የታየ በመሆኑ ሥራ አጦችን ወደ ሥራ ለማስገባትና በኢኮኖሚ ተጠቃሚ ለማድረግ በቅንጅት መሥራት አማራጭ የሌለው ጉዳይ መሆኑ ተመልክቷል።

የጌዴኦ ዞን የሥራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕሪይዞች ልማት መምሪያ  ኃላፊ አቶ ተገኝ ታደሰ የመስሪያና የመሸጫ ቦታዎችን ከማመቻቸት አኳያ ውስንነቶች መስተዋላቸውንና የብድር አመላለስና ስርጭት ላይ በቅንጅት በመሥራት የዜጎችን የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ይኖርብናል ነው ያሉት።

በመድረኩ የጌዴኦ ዞን  የብልፅግና  ፓርቲ  ጽህፈት ቤት ኃላፊና የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ አበባየሁ ኢሳያስ በበኩላቸው የሕዝባችንን የኢኮኖሚ ችግር በመፈታትና የሥራ ዕድል ለመፍጠር በሚያመች መልኩ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ ሁሉም ባለድርሻ አካላት በቅንጅት ሊሰራ እንደሚገባ አመላክተዋል።

በቀጣይም በቁጠባና በብድር አመላለስ ላይ የተጀመሩ የፖሊሲ ማስተካከያዎች ያሉ በመሆኑ   በአጭር ጊዜ ውስጥ የዜጎችን ኢኮኖሚ ለማሳደግ የተጠናቀሩ መረጃዎችን በማጥራት ችግሮቹን በዘላቂነት መፍታት ይጠበቃል ብለዋል።

በመድረኩ የዞኑ የብልጽግና ፓርቲ የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ አበባየሁ ኢሳያስና የዞኑ የሥራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዞች ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ ተገኝ ታደሰን ጨምሮ ሌሌችም የዞኑ አስፈፃሚ አካላት እና ጥሪ የተደረጉላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።

ዘጋቢ: ፅጌ ደምሴ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን